ደቡብ አፍሪካ በዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ በመወሰድ ከኤችአይቪ ቫይረስ አስቀድሞ የሚከላከልለውን “ሌናካፓቪር” የተሰኘ መድኃኒት በሀገር ውስጥ ለማምረት የሚያስችል አምራች ድርጅት የመለየት ሥራ መጀመሯ ተሰማ።
የጊሊያድ ሳይንስ ኩባንያ ምርት የሆነውን ይህንን ዘመናዊ መድኃኒት ለማምረት፤ መንግሥት ከዩኒታይድ እና ከአሜሪካ ፋርማኮፒያ ጋር በመተባበር ብቁ የሆኑ የሀገር ውስጥ ኩባንያዎችን በመገምገም ላይ ይገኛል።
በአሁኑ ወቅት በሕንድ፣ ግብፅ እና ፓኪስታን ለሚገኙ ስድስት ኩባንያዎች የማምረት ፈቃድ የተሰጠ ሲሆን፣ ደቡብ አፍሪካ ሰባተኛዋ ባለፈቃድ ለመሆን ጥረት እያደረገች ነው።
በዓለም ከፍተኛው የኤችአይቪ ስርጭት ያለባት ደቡብ አፍሪካ፣ መድኃኒቱን በሀገር ውስጥ ማምረቷ ቫይረሱ ወደ ሌሎች እንዳይተላለፍ ለመከላከልና ለአጠቃላይ የአፍሪካ ቀጣና መድኃኒቱን በግማሽ ዋጋ ለማቅረብ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል።
ይህ እርምጃ ሀገሪቱ በጤናው ዘርፍ ራሷን ለመቻልና ወረርሽኙን ለመቆጣጠር ለምታደርገው ጉዞ ወሳኝ ምዕራፍ ተደርጎ ተወስዷል።
