በ”ፊንቴክ” ኢንቨስትመንት ስም በተፈጸመ የማጭበርበር ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የዋሉ ታዋቂ አርቲስቶች እና የቲክቶክ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ዛሬ ሚያዝያ 9 ቀን 2018 ዓ.ም በፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቀርበዋል።
ፍርድ ቤቱ ለዛሬ ቀጠሮ ሰጥቶ የነበረው ፖሊስ ክስ ለመመስረት የሚያስችለውን ምርመራ አጠናቆ እንዲያቀርብ ነበር።
መርማሪ ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ስር ከዋሉበት ጊዜ ጀምሮ ያከናወናቸውን የምርመራ ተግባራት ለችሎቱ በዝርዝር አስረድቷል።
ይሁን እንጂ የወንጀሉ ድርጊት ውስብስብነትና ስፋት ከፍተኛ መሆኑን፤ የተጭበረበረው የገንዘብ መጠንና የተጎጂዎች ቁጥር መበራከቱ ፣ቀሪ ምስክሮችን ለመስማትና የሰነድ ማስረጃዎችን ለማሰባሰብ ጊዜ እንደሚያስፈልገው በመጥቀስ፤ ተጨማሪ የ14 ቀናት የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ፍርድ ቤቱን ጠይቋል።
የተጠርጣሪዎች ጠበቆች በበኩላቸው
ተጠርጣሪዎቹ በሕዝብ ዘንድ የሚታወቁና ቋሚ መኖሪያ ያላቸው በመሆኑ አይሰወሩም፣
ከተጠርጣሪዎቹ መካከል የጤና እክል ያለባቸው ስላሉ በውጭ ሆነው ጉዳያቸውን ቢከታተሉ፣ የራሳቸው የሆነ መደበኛ መተዳደሪያ ሥራ ያላቸው መሆኑም ታሳቢ እንዲደረግላቸው ጠይቀዋል።
ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ካዳመጠ በኋላ ውሳኔ ለመስጠት ለሚያዝያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
