በመቅደላ ጦርነት ጊዜ የተዘረፉ የአጼ ቴዎድሮስ የፀጉር ቁንዳል እና የልብስ ቁራጮች እንዲሁም የወርቅ አምባር ቅርሶች ከ158 ዓመታት በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰዋል፡፡
ቅርሶቹ የተመለሱት ከእንግልዝ ሀገር ሲሆን ቅርሶቹን ያመጡት ሮቢን ጃክሴን (ዶ/ር) የእንግልዝ የንግስቲቱ ቤተሰብ ሙዚየም ኃላፊና አሉላ ፓንክረስት (ዶ/ር ) የኢትዮጵያ ቅርስ አስመላሽ ኮሚቴ አባልና ተመራማሪ ናቸው፡፡
የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አበባው አያሌው እና የኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር አባላት ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት በመገኘት ለቅርሶቹ ደማቅ አቀባበል አድርገዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አበባው አያሌው ታሪካዊ የሆኑ ቅርሶች በተለያዩ ምክንያቶች ከሀገር ውጭ የወጡትን ወደ ኢትዮጵያ የመመለስ ስራ በትልቅ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን አብራርተው በተለይ በዘንድሮ ዓመት አመርቂ የሆነ ስራ የተሰራበት ዓመት ነው፣ ትልቅ የዲፕሎማሲ ስኬትም የተገኘበት ዓመት ነው ብለዋል፡፡
ወደ ኢትዮጵያ የገቡት ቅርሶች ግንቦት 7/2018ዓ.ም በባለስልጣን መ/ቤቱ የቅርሶቹ ርክክብ እንደሚደረግ የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ተናግሯል፡፡
