የአፍሪካ ልማት ባንክ ለአፍሪካ ንግድ እና ኢንቨስትመንት ልማት ኢንሹራንስ (ATIDI) የ125 ሚሊዮን ዶላር ካፒታል እንደሚያፈስ አስታወቀ።
ይህ እርምጃ ባንኩ የተቋሙ ትልቁ ባለድርሻ እንዲሆን የሚያደርገው ሲሆን፣ የግል ካፒታልን ወደ አህጉሪቱ ለመሳብ የሚሰጠውን የዋስትና አቅም ለማሳደግ ያለመ ነው።
ባለፈው መስከረም ወር የባንኩ ፕሬዝዳንት ሆነው የተሾሙት ሲዲ ኡልድ ታህ እንደገለጹት፣ ከበለጸጉ አገራት የሚገኘው የልማት ዕርዳታ ባለፈው ዓመት በአንድ አራተኛ ገደማ በመቀነሱ አህጉሪቱ አዲስ የፋይናንስ ሞዴል መከተል አስገድዷታል።
ይህ አዲስ የኢንቨስትመንት ስትራቴጂ “የአፍሪካ አዲስ የልማት ፋይናንስ መዋቅር” (NAFAD) አካል ሲሆን፣ በየዓመቱ የሚታየውን የ400 ቢሊዮን ዶላር የልማት ፋይናንስ ክፍተት ለመሙላት ታስቧል።
እቅዱ በአፍሪካ ውስጥ በተበታተነ መልኩ የሚገኙትን የጡረታ ፈንዶች፣ የሉዓላዊ ሀብት ፈንዶች እና የቁጠባ እቅዶችን ጨምሮ 4 ትሪሊዮን ዶላር የሚገመተውን የአገር ውስጥ ካፒታል በቅንጅት ጥቅም ላይ ማዋልን ያለመ ነው።
በዚህ አዲስ መዋዕለ ንዋይ አማካኝነት የአፍሪካ ልማት ባንክ በኤጀንሲው (ATIDI) ውስጥ ያለው የባለቤትነት ድርሻ ከ3 በመቶ ወደ 14 በመቶ ከፍ ይላል።
ባንኩ በየዓመቱ በተቋሙ በኩል የሚሰጠውን የዋስትና መጠን ወደ 10 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ያቀደ ሲሆን፣ ይህም ቀደም ሲል ከነበረው የ3 ቢሊዮን ዶላር አማካይ ዓመታዊ ዋስትና አንጻር ሲታይ የኤጀንሲውን ዓመታዊ የዋስትና መጠን በሦስት እጥፍ ያሳድገዋል ተብሎ ይጠበቃል።
capital
