የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከካናዳው ታዋቂ አውሮፕላን አምራች ዴ ሃቪላንድ ከገዛቸው ሁለት DHC-6 Twin Otter Classic 300-G ዘመናዊ አውሮፕላኖች መካከል የመጀመሪያዋን በይፋ ተረክቧል።
ይህ አዲስና ሁለገብ አውሮፕላን በሀገሪቱ የተለያዩ ክልሎች መካከል ያለውን የትራንስፖርት ትስስር ይበልጥ ለማጠናከር ታስቦ የተዘጋጀ ሲሆን፣ በተለይም ለአስቸጋሪ የአየር ንብረትና አጫጭር የአውሮፕላን ማረፊያ መንገዶች ፍጹም ተመራጭ መሆኑ አየር መንገዱን ይበልጥ ተወዳዳሪ ያደርገዋል።
ይህ ዘመናዊ አውሮፕላን መደበኛ የመንገደኞች በረራን ከማሳለጥ ባለፈ፣ በሀገሪቱ የቱሪዝም እንቅስቃሴ ላይ ትልቅ መነቃቃትን ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል።
በተጨማሪም ለአየር ላይ ቅየሳና ጥናቶች እንዲሁም በአስቸኳይ ጊዜ ህይወት አድን አገልግሎት ለሚሰጡ የአየር ላይ አምቡላንሶች የሚውል በመሆኑ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተለያዩ የገበያ ፍላጎቶችን በላቀ ብቃት፣ በታማኝነትና በአስተማማኝ ሁኔታ ለማገልገል ያለውን አቅም ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋግረዋል።
