የመልክዕክት መለዋወጫ መተግበሪያ የሆነው ዋትስአፕ፤ ተጠቃሚዎች ‘ዩዘርኔም’ ብቻ በመለዋወጥ ቁጥራቸውን ሳይታወቅ ከሰዎች ጋር እንዲነጋገሩ ሊፈቅድ ነው።
በዓለም አቀፍ ደረጃ ሦስት ቢሊዮን ተጠቃሚዎች ያሉት ዋትስአፕ፤ ይህ አሠራር በሚቀጥሉት ጥቂት ወራት ውስጥ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንደሚሆን ገልጿል።
ከዚህ ሳምንት ጀምሮ ግን ተጠቃሚዎች መለያ የሚሆናቸውን ‘ዩዘርኔም’ እንዲመርጡ ፈቅዷል። ይህንን መለያ ማስቀመጥ ግዴታ እንዳይሆን ተነግሯል።
ተቋሙ እንደገለጸው፤ ተጠቃሚዎች ባሻቸው ጊዜ ‘ዩዘርኔሙን’ ማጥፋት ወይም መቀየር ይችለሉ።
አሠራሩ ተግባራዊ መሆን ሲጀምር የዋትስአፕ ተጠቃሚዎች ‘ዩዘርኔም’ ብቻ በመለዋወጥ ከሰዎች ጋር መነጋገር ይችላሉ። የማይፈለጉ መልዕክቶችን ‘ብሎክ’ የማድረጊያ አማራጭ አሁንም ቢሆን ይቀጥላል።
ተጠቃሚዎች የሚመርጡት ስም ከ35 ፊደላት ያነሰ መሆን አለበት። እጅግ ታዋቂ የሆኑ ሰዎችን ስም ግን ሌሎች ተጠቃሚዎች እንዲጠቀሙበት አይፈቀድም።
