ሐሙስ ግንቦት 7/2017 ዓ.ም በትግራይ ደቡባዊ ዞን ማይጨው ከተማ የደብረፅዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) ህወሓት ባላፈው ሳምንት የሰጠውን ጋዜጣዊ መግለጫ የሚቃወም ሰልፍ ተካሄደ።
ትናንት ግንቦት 6/2017 ዓ.ም ከኢትዮጵያ የፓለቲካ ፓርቲዎች የተሰረዘው ህወሓት ሊቀመንበር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) ባለፈው ሳምንት ወይን ለተባለ የድርጅታቸው ልሳን በሰጡት ቃል ” ድርጅታቸው በክልሉ ደቡባዊ ዞን የአመራር ማስተካከያ እንደሚያካሂድ ” ዝተው ነበር።
የዞኑ አስተዳደር በመራውና ባስተባበረው ዛሬ በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ የሊቀ-መንበሩን መግለጫ ሙሉ በሙሉ በመቃወም ቡድኑ ያሰበውን ከመፈፀም እንዲቆጠብ የሚያስጠነቀቁ የቁጣ ድምፆች ተሰምተዋል።
በሰልፉ ፦
– ምርጫችን ሰላም ነው !
– አስተዳደራችን ለሚነካ የህወሓት ከፋይ ቡድን አንታገስም !
- ኋላቀር አስተሳሰብን እንቃወማወለን !
– የሻእቢያ ተልእኮ ከሚያስፈፅም ሃይል ግንኙነት የለንም ! - በምስለኔ አንመራም !
የሚሉና ሌሎች መፈክሮች ተደምጠዋል።
በሰላማዊ ሰልፉ የተገኙ ዳግም ጦርነት አንዳይንቀሳቀስ ስጋት ያደረባቸው እናቶች በምህላና እንባ መሬት ላይ ተኝተው ሲማጸኑ ታይተዋል።
በሰላማዊ ሰልፉ በመገኘት መልእክት ያስተላለፉት የማይጨው ከተማ ከንቲባ ዮሃንስ አዱኛና የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ሃፍቱ ኪሮስ ፤ ህዝቡ ሰላሙ እንዳይነጠቅ ከማንኛውም ጊዜ በላይ ንቁ መሆን አለበት ብለዋል።
ሰልፉ ከትናንት የህወሓት ስረዛ ተያያዥነት የሌለው ቀድሞ የተያዘ ፕሮግራም እንደሆነ ቲክቫህ ኢትዮጵያ የመቐለ ቤተሰብ አረጋግጧል።
ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች የተወጣጡ ተሳታፊዎች ያካሄዱትን ሰልፍ በሰላም ማጠናቀቃቸውን ቲክቫህ ኢትዮጵያ ከማይጨው ኮሙኒኬሽን ፅህፈት ቤት ያገኘው መረጃ ያሳያል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
መቐለ
