ፓርቲዎቹ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) እና የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሲሆኑ የኦሮምያ ክልል መንግስት ፀጥታን ጨምሮ በተለያዩ ጉዳዮች እንዲያወያያቸው ጥያቄ አቅርበዋል።
ፓርቲዎቹ ህዳር 9 ቀን 2018 ዓ.ም በፃፉት የእንወያይ ጥያቄ ደብዳቤ ከክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ጋር ስለኦሮምያ እና ኦሮሞ ህዝብ ለመወያየት ቀጠሮ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።
የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ ሊቀመንበር ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና እንደገለፁት የውይይቱን አጅንዳ በዝርዝር ይሁንታን ካገኙ በኋላ እንደሚገልፁ ጠቅሰው በጥቅሉ በኦሮሚያ ክልል አሁናዊ ተጨባጭ ሁኔታዎች ላይ ለመወያየት እቅድ እንዳላቸው ጠቁመዋል።
ፕሮፌሰሩ ውይይቱ በዋናነት በክልሉ የሰላም ችግር እና ሌሎች በክልሉ ችግሮች ላይም ውይይት እናደርጋልን ብለው ዝርዝር መረጃዎች ዉይይቱ ሲጀመር እንደሚገልፁልን ተናግረዋል።
በተመሳሳይ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ቃል አቀባይ አቶ ለሚ ገመቹ እንደተናገሩት የውይይቱ አጅንዳዎች ለክልሉ መንግስት የቀረበው ጥያቄ ምላሽ ካገኘ በኃላ እንደሚገለፅ ነው።
የክልሉ የሰላም ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ በመሆኑ ዋና የመወያያ ነጥብ መሆኑን ጠቅሰው የመወያያ ዝርዝር ነጥቦችን ግን ከመግለፅ ተቆጥበዋል። ይህ የህዳር 9 ቀን 2018 ዓ.ም የእንወያይ ጥያቄ ደብዳቤ ከስድስት አመት በኋላ ኦነግ ያቀረበው ጥሪ መሆኑም ተገልጿል።
ሁለቱም ፓርቲዎች የክልሉን መንግስት ምላሽ እየተጠባበቁ ቢሆንም ይህ የእንወያይ ጥያቄን ተከትሎ እስካሁን ከክልሉ መንግሥት የተሰጠ ምንም ምላሽ የለም። ከቲክቫህ
