የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (ሲፒጄ)፣ በሽብርተኝነት ወንጀል የተከሰሱ አራት ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች ፍትሐዊ፣ ግልጽ እና ሕጋዊ ሥርዓቱን የጠበቀ የፍርድ ሂደት እንዲያገኙ አሳሰበ።
ድርጅቱ የካቲት 17 ቀን 2018 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ፣ ጋዜጠኛ ጎበዜ ሲሳይ፣ መስከረም አበራ፣ ገነት አስማማው እና ዳዊት በጋሻው አስፈላጊው የሕግ ጥበቃ ሊደረግላቸው እንደሚገባ አሳስቧል።
ድርጅቱ እነዚህ ጋዜጠኞች በአማራ ክልል ከነበረው አለመረጋጋት ጋር ተያይዞ በሰሩት ዘገባዎች ምክንያት በቁጥጥር ስር ውለው ላለፉት ሦስት ዓመታት ገደማ በእስር ላይ ይገኛሉ ብሏል።
ከእነዚህ መካከል “የአማራ ድምፅ” ሚዲያ መስራች ጋዜጠኛ ጎበዜ ሲሳይ፣ እ.ኤ.አ ግንቦት 2023 በጅቡቲ በቁጥጥር ስር ውሎ ወደ ኢትዮጵያ ተላልፎ መሰጠቱ ይታወሳል ሲል አክሏል።
የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በቅርቡ በሰጠው ብይን፣ ዐቃቤ ሕግ ያቀረበው ማስረጃ ተከሳሾቹን ለመከላከል የሚያበቃ ነው በማለቱ፣ ጋዜጠኞቹ በመጪው ግንቦት ወር መከላከያቸውን ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የ“ኢትዮ ንቃት” ሚዲያ መሥራች እና አዘጋጅ መስከረም አበራ፣ የ“የኛ” ሚዲያ ሪፖርተር ገነት አስማማው እና የ“አራት ኪሎ” ሚዲያ አዘጋጅ ዳዊት በጋሻው ከሌሎች አምስት ጋዜጠኞች ጋር በመሆን እ.ኤ.አ በሚያዝያ 2023 መጀመሪያ ላይ መታሰራቸው ይታወሳል።
ሲፒጄ በመግለጫው፣ ጋዜጠኞቹ ለረጅም ጊዜ በእስር መቆየታቸው እና የቀረበባቸው ክስ ክብደት በኢትዮጵያ ያለውን የፕሬስ ነፃነትን አደጋ ላይ የሚጥል መሆኑን ገልጿል። በመሆኑም የኢትዮጵያ መንግስት ዓለም አቀፍ የፍትሐዊ የፍርድ ሂደት መስፈርቶችን እንዲያከብው ጥሪ አቅርቧል።
