የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ነዋሪዎች ባሉበት ቦታ ሆነው በሞባይል ስልካቸው የሚያገኙትን አገልግሎቶች ቁጥር እንደሚጨምር አስታውቋል።
ተቋሙ ባለፈው ሳምንት ይፋ ያደረገው ዐዲስ አገልግሎት የከተማዋ ነዋሪዎች በሞባይል ስልካቸው መታወቂያቸውን ማሳደስ፣ የልደት ሰርተፍኬት ማውጣት፣ መታወቂያቸውን ከፋይዳ ጋር የማስተሳሰር፣ ያላገቡ መሆናቸውን የሚያረጋግጡበት ሰርተፍኬት የሚሉ 4 አገልግሎቶች ናቸው።
በቀጣይ በዚህ አገልግሎት የጋብቻ እና የፍቺ ሰነዶችን በሞባይል ስልክ ማመልከት የሚቻልበት አሠራር እንደሚጀመር የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮሴፍ ንጉሴ ተናግረዋል።
አሁን ላይ ዐዲሱ አገልግሎት ለአዲስ የከተማዋ ነዋሪ ተመዝጋቢዎች የሚሰራ አለመሆኑን ገልጸው መሸኛ በማቅረብ መታወቂያ ለመውሰድ የሚፈልጉ ዜጎችም ወደፊት አገልግሎቱን በእጅ ስልካቸው የሚያገኙበት አሠራር እንደሚጀመር ገልጸዋል።
የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ነዋሪዎች ባሉበት ሆነው በእጅ ስልካቸው የሚያገኟቸው 4 አገልግሎቶች ወረፋ የሚበዛባቸው እንደሆኑ ገልጿል።
ነዋሪዎች የሚፈልጉትን አገልግሎት ካመለከቱ በኋላ ክፍያውን በቴሌብር እንደሚፈጽሙ ተገልጿል። የጠየቁት አገልግሎት ሲፈጸም በሚደርሳቸው መልዕክት ባመለከቱበት ወረዳ በመሄድ መረከብ ይችላሉ::
አሐዱ ራዲዮ
