በሶማሊያ ዋና ከተማ ሞቃዲሾ ለወታደራዊ ምዝገባ ተሰልፈው የነበሩ ታዳጊዎች ላይ በደረሰ የቦምብ ጥቃት ቢያንስ 10 ታዳጊዎች መሞታቸው ተገለጸ፡፡
ታዳጊዎቹ የተገደሉት ዳማንዮ በተባለ ወታደራዊ ካምፕ ላይ የአልሸባብ አሸባሪ ቡድን ባደረሰው ጥቃት መሆኑም ተዘግቧል፡፡
አሸባሪ ቡድኑ ባወጣው መግለጫም ከጥቃቱ ጀርባ እጁ እንዳለ እና እስከ 30 የሚደርሱ ወታደሮችን መግደሉን እንዲሁም ሌሎች 50 ሰዎች ማቁሰሉን ገልጿል።
አልሻባብ በሚጠቀምበት የሬዲዮ ጣቢያ በርካታ አዲስ ምልምል ወታደሮችን ገድለናል ማለቱን እንዲሁም በጥቃቱ ከተገደሉት በተጨማሪ 16 ሰዎች መጎዳታቸውን የሀገሪቱን ፖሊስ ዋቢ አድርጎ የጀርመን ዜና አገልግሎት ዲፒኤ ዘግቧል።
በጥቃቱ ብርቱ ጉዳት ደርሶባቸው በአስጊ ሁኔታ ውስጥ ያሉ በርካቶች መሆናቸውን ተከትሎ የሟቾች ቁጥር ሊያሻቅብ እንደሚችል ተገምቷል።
