የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አገልግሎት (ኢባትሎ) በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት 108.78 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱን የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር በሪሶ አመሎ አስታወቁ። ይህ ገቢ ድርጅቱ ካቀደው 101.86 ቢሊዮን ብር በ107 በመቶ ብልጫ ያለው መሆኑ ተገልጿል።
ዶ/ር በሪሶ ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቁት፣ ኢባትሎ በበጀት ዓመቱ 3.7 ሚሊዮን ቶን ገቢ ጭነት እና 40 ሺህ ቶን ወጪ ጭነት በራሱና በኪራይ መርከቦች አጓጉዟል። በተጨማሪም 108 ሺህ TEU ኮንቴይነሮችን በመልቲሞዳል ሲስተም እንዲሁም 2.2 ሚሊዮን ቶን ገቢ ጭነት እና 356 ሺህ ቶን ወጪ ጭነት በዩኒሞዳል ሲስተም ማጓጓዙን ገልጸዋል።
በአጠቃላይ 437 ሺህ TEU ኮንቴይነሮች በደረቅ ወደቦችና ተርሚናሎች መስተናገዳቸውን አስታውቀዋል።
ዋና ስራ አስፈጻሚው በቀይ ባህር አካባቢ የነበረው የጸጥታ ችግር ፈተና እንደነበር የገለጹ ሲሆን፣ ድርጅቱ የራሱን መርከቦች የጉዞ መስመር በማጠፍ እና ሌሎች ስትራቴጂዎችን በመተግበር ጭነቶችን በተፈለገው ፍጥነት ማጓጓዝ እንደቻለ አብራርተዋል።
ለተገኘው ከፍተኛ ገቢ የሀገር በቀል ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሚና እንደነበረው የገለጹት ዶ/ር በሪሶ፣ ድርጅቱ የውጭ ምንዛሪ ገቢን ለማሳደግ በሌሎች አገራት ወደቦች መካከል የሚሰጠው የጭነት ማጓጓዣ አገልግሎት፣ የዲጂታላይዜሽን ስራዎች፣ የባቦጋያ ማሪታይምና ሎጅስቲክስ ስልጠና አገልግሎት እድገት አስተዋፅኦ ማበርከታቸውን ጠቅሰዋል።
CapitalNews
