የኢትዮጵያ ግብርና ባለሥልጣን ከ2017 እስከ 2018 ዓ.ም. ባሉት ሁለት ዓመታት ከ2ሺህ 600 በላይ ኩባንያዎች እንደ ሰሊጥ፣ ቡና፣ ፍራፍሬ እና ሌሎች ምርቶቻቸውን ወደ ቻይና ገበያ ለማሰገባት የሚያስችላቸውን ምዝገባ ማከናወናቸውን አስታውቋል።
የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ወንዳላ ሐብታሙ እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ እስካሁን ምርቶቿን ወደ ቻይና የምትልከው ወጥ በሆነ አሰራር ሳይሆን በነጋዴዎች ፍላጎት ላይ በመመስረት ነበር።
በርካታ ሀገራት ለኤክስፖርት ፈቃድ የሚሰጡት ለ6 ወር ወይም ለአንድ ዓመት ብቻ መሆኑን የገለጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፣ በቻይና አሰራር ግን አንድ ጊዜ የተገኘ የወጪ ንግድ (ኤክስፖርት) ፈቃድ ለ5 ዓመታት እንደሚያገለግል ተናግረዋል።
ወደ ቻይና የሚላከው ምርት በከፍተኛ መጠን እንዳደገ የገለጹት ዶክተር ወንዳላ፣ ባለሥልጣኑ አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረግ በርካታ ለውጦችን እያመጣ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
በኢትዮጵያ የሚላኩ ሁሉም ምርቶች ዓለም ባቀመጠው መስፈርት መሰረት መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፣ በተለይ የእጽዋት ንግድ ሥርዓቱ በ47 አንቀጾች የተዋቀረ እንደሆነ አስገንዝበዋል።
አሐዱ ሬዲዮ
