የዓለም ባንክ ግሩፕ በኢትዮጵያ በሚካሄደው የኃይል መሠረተ ልማት ግንባታ ላይ “በተንኮል እና በማጭበርበር ድርጊቶች” ተሳትፈዋል ያላቸው ሦስት የፕራይስዋተርሃውስ ኩፐርስ (PwC) የአፍሪካ ቅርንጫፎች ላይ የ21 ወራት እገዳ መጣሉን በይፋ አስታወቀ።
እገዳው የተጣለባቸው በሞሪሸስ የሚገኘው ፒ.ደብሊው.ሲ አሶሲዬትስ አፍሪካ፣ ፒ.ደብሊው.ሲ ኬንያ እና ፒ.ደብሊው.ሲ ሩዋንዳ ላይ እንደሆነ ባንኩ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል።
እንደ ዓለም ባንክ ከሆነ፣ ኩባንያዎቹ ለእገዳ የበቁት በኢትዮጵያ እና በኬንያ መካከል ያለውን የኤሌክትሪክ ትስስር ለመፍጠር በሚንቀሳቀሰው “የምስራቅ አፍሪካ የኤሌክትሪክ ሀይዌይ ፕሮጀክት” ላይ በተፈጸመ የሥነ-ምግባር ጉድለት ነው።
ኩባንያዎቹ እ.ኤ.አ. በ2019 የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያወጣውን የዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሪፖርት አቀራረብ ደረጃዎች ትግበራ የምክር አገልግሎት ውል ለማሸነፍ ሲሉ፣ ከፕሮጀክቱ ባለሥልጣናት ጋር በመመሳጠር ሚስጥራዊ የሆኑ የጨረታ መረጃዎችን ማግኘታቸው ተረጋግጧል።
በተጨማሪም ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በሚከናወን የቋሚ ንብረት ቆጠራ እና ግምገማ ውል ላይ የባለሙያዎችን ብቃትና ልምድ በተመለከተ የሐሰት መረጃ ማቅረባቸው ነዉ የተገለፀው።
ፒ.ደብሊው.ሲ አፍሪካ የተሰኘውና የቅርንጫፎቹን እንቅስቃሴ የሚቆጣጠረው ተቋም፣ ምንም እንኳን እሱ ራሱ እገዳ ባይጣልበትም፣ ቅርንጫፎቹ የቀረበባቸውን የሥነ-ምግባር ግዴታዎች እንዲያከብሩ ክትትል ለማድረግ ስምምነቱን በዋስትና መፈረሙ ተመላክቷል።
