በኢትዮጵያ በፍጥነት እያደጉ ከሚገኙ እና ከፍተኛ የባለአክስዮኖች ቁጥር ካላቸው ባንኮች አንዱ የሆነው አማራ ባንክ፣ አቶ ይህንዓለም አቅናውን በዋና ስራ አስፈፃሚነት መሾሙን አስታውቋል።
የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ጥብቅ መስፈርቶችን በማስቀመጥ ባደረገው እጩዎች ግምገማ፣ አቶ ይህንዓለም በትምህርት ዝግጅታቸውና በኢንዱስትሪው ውስጥ ባላቸው የረጅም ጊዜ ልምድ ለቦታው መብቃታቸውን ገልጿል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክም ሹመታቸውን አጽድቋል።
አዲሱ ዋና ስራ አስፈጻሚ በዳሸን ባንክ ከጀማሪ ባለሙያነት እስከ ከፍተኛ የአመራር እርከን ባገለገሉባቸው ከ25 ዓመታት በላይ የሥራ ዘመናቸው የቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ፣ የብድር እና የስትራቴጂ መምሪያ ዳይሬክተር፣ እንዲሁም ዋና መኮንን በመሆን አገልግለዋል።
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በሂሳብ አያያዝ የመጀመሪያ ዲግሪ፣ በኢንፎርሜሽን ሲስተምስ ሁለተኛ ዲግሪ እና በሥራ አመራር ማስተርስ ዲግሪ ያላቸው ሲሆን፣ ከዩናይትድ ኪንግደም የኤ.ሲ.ሲ.ኤ ማረጋገጫም እንዳላቸው ተገልጿል።
አቶ ይህንዓለም የአማራ ባንክን የአመራር ቦታ የተረከቡት መስከረም 2017 ላይ በዋና ሥራ አስፈፃሚነት ተሹመው ለአንድ ዓመት ከአራት ወራት ገደማ ያገለገሉትንና በየካቲት 2018 ላይ ፀደይ ባንክን የተቀላቀሉትን ዮሐንስ አያሌዉን በመተካት ነው።
