አውስትራሊያ ከ16 ዓመት በታች የሆኑ ህፃናት የማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም በይፋ አገደች። ሀገሪቱ ከ16 ዓመት በታች ለሆኑ ሕፃናት ማኅበራዊ ሚዲያን በመከልከል የዓለማችን የመጀመሪያዋ ሀገርም ሆናለች ።
አውስትራሊያ ከዛሬ ጀምሮ ከ16 ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት ማኅበራዊ ሚዲያዎችን እንዳይጠቀሙ የሚከለክለው አዲስ ህግ ተግባራዊ ማድረግም ጀምራለች ።
ሕጉ ባለፈው ዓመት በፓርላማ የጸደቀ ሲሆን ከ16 ዓመት በታች የሆኑ አውስትራሊያዊያን አካውንት እንዳይፈጥሩ ወይም እንዳይይዙ እና ገደብ የተጣለባቸው ማኅበራዊ ሚዲያዎች ተገቢ እርምጃዎችን እንዲወስዱ ያስገድዳል።
ይህ ታሪካዊ እርምጃ እንደ ስናፕቻት ፣ቲክቶክ፣ ዩቲዩብ ፣ ኢንስታግራም እና ፌስቡክ ያሉ ግዙፍ የማህበራዊ ሚዲያ ኩባንያዎች ላይ ያነጣጠረ ነው። ኩባንያዎቹ እገዳውን ለማስፈጸም ተገቢ እርምጃዎችን መውሰድ ካልቻሉ እስከ 49.5 ሚሊዮን የአውስትራሊያ ዶላር ወይም 33 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሚደርስ ከባድ ቅጣት ይጠብቃቸዋል።
መንግሥት ይህንን እርምጃ የወሰደው ሕፃናትን “በእድገታቸው ወሳኝ ምዕራፍ” ላይ ከማህበራዊ ሚዲያ አሉታዊ ተጽእኖ ለመጠበቅ እንደሆነ ገልጿል።
የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኔዝ ባስተላለፉት የቪዲዮ መልዕክት ማኅበራዊ ሚዲያ ፣ ማኅበራዊ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን እናውቃለን ያሉ ሲሆን ይህ ሕግ የልጆቻችንን ደኅንነት ይጠብቃል ሲሉ ተናግረዋል።
ይህ አዲስ ህግ ተግባራዊ መሆኑን ተከትሎ በህዝቡ ውስጥ ክፍፍል የፈጠረ ሲሆን ወላጆች እና የህጻናት ተሟጋቾች ህጉን በሰፊው ሲደግፉ ወጣቶች፣ ታዳጊዎችና የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ተቃውመውታል ።
ሕጉን የማይታወቅ እና ችግር ያለበት እንዲሁም በችኮላ የወጣ ነው ሲሉ ግዙፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች እገዳውን በጽኑ የተቹ ሲሆን ህጉን መተግበር አዳጋች እንደሆነ እና ህፃናት በድብቅ አካውንት እንዲከፍቱ ሊገፋፋ ይችላል ሲሉም ስጋታቸውን ገልጸዋል።
ሜታ እና ቲክቶክ ሕጉን ለማስፈጸም አስቸጋሪ እንደሚሆንባቸው ቢገልጹም የወጣውን ህግ ለማክበር ቃል ገብተዋል። የፌስቡክና ኢንስታግራም ባለቤት ሜታ ቀነ ገደቡ ከመድረሱ በፊት ከ16 ዓመት በታች የሆኑ አካውንቶችን ማስወገድ መጀመሩ ተገልጿል።
አውስትራሊያ በወሰደችው በዚህ እርምጃ ሌሎች ሀገራት ተመሳሳይ ሕጎችን እንዲያወጡ ግፊት ይፈጥራል እየተባለም ይገኛል።
ዘገባው የቢቢሲ ነው
በ -ሰላማዊት ወልደገሪማእ
