የባሕረ ሰላጤው ትብብር ምክር ቤት አባል አገራት መሪዎች የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በአካል ሳዑዲ አረቢያ ውስጥ ሊሰበሰቡ መሆኑን ሮይተርስ ዘገበ።
የመሪዎቹ ስብሰባ የሚያተኩረው ሁለት ወር በሞላው ጦርነት ለዘነቡባቸው በሺህዎች የሚቆጠሩ የኢራን የሚሳዔል እና ድሮን ጥቃቶች ምላሽ ማዘጋጀት ላይ እንደሚሆን ዜና ወኪሉ ምንጮች ጠቅሶ ዘግቧል።
በአሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት የተከፈተባት ኢራን በስድስቱም የባሕረ ሰላጤው ትብብር ምክር ቤት አባል አገራት የሚገኙ የኤነርጂ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት ፈጽማለች።
ከአሜሪካ ጋር ግንኙነት ያላቸው ተቋማት እና ሌሎች የሲቪል መሠረተ ልማቶችን እንዲሁም ወታደራዊ ይዞታዎችንም አጥቅታለች።
ሮይተርስ የጠቀሰው የሳዑዲ መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገባ እንደሚያመለክተው የኳታር፣ ኩዌት እና ባህሬን መሪዎች እንዲሁም የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በስብሰባው ለመሳተፍ ጅዳ ገብተዋል።
የምክር ቤቱ አባል የሆነችው ኦማን በማን እንደምትወከል እስካሁን አለመታወቁም ተጠቅሷል።
የባሕረ ሰላጤው ምክር ቤት ለጦርነቱ በቂ ምላሽ አልሰጠም በሚል ከኤምሬቶች ትችት ቀርቦበት ነበር።
