የቤላሩስ ፕሬዝዳንት አሌክሳንደር ሉካሼንኮ ከኢትዮጵያ ጋር የሁለትዮሽ ግንኙነትን ለማጠናከር ሀገራቸው ቁርጠኛ መሆኗን አስታወቁ። በተለያዩ ዘርፎች ትብብርን ለማስፋት ጠንካራ “ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ፍላጎት” እንዳላቸውም ገልጸዋል።
“ኢትዮጵያ ለእኛ በምስራቅ አፍሪካ ከሚገኙት በጣም አስፈላጊ አገሮች መካከል አንዷ ናት” ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ቤላሩስ የቴክኖሎጂ፣ የግብርና እና የምህንድስና ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።
ፕሬዚዳንቱ ቤላሩስ ለኢትዮጵያ የግብር ማሽነሪዎችን ድጋፍ ለማድረግ፣ ቴክኖሎጂን ለማስተላለፍ እና የኢትዮጵያ ባለሙያዎችን ለማሰልጠን ዝግጁ መሆኗንም ገልጸዋል።
በጥቅምት ወር የቤላሩሱ መሪ ኢትዮጵያ የባህር መዳረሻ ለማግኘት ያላትን ፍላጎት በብርቱ ደግፈዋል። የሀገሪቱ ሚዲያ እንደዘገበው፤ ሉካሼንኮ የኢትዮጵያን የባህር በር የማግኘት ፍላጎትን የሚቃወሙ “ፍጹም ሞኞች” ናቸው ብለዋል።
አክለውም “በጦርነት ወይም በድርድር ኢትዮጵያ ወደ ባህር በር ትደርሳለች። በእርግጥም በሰላማዊ መንገድ ቢሆን የተሻለ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።
