በኢትዮጵያ የሳተላይት ቴሌቪዥን ታሪክ ውስጥ ቀዳሚና ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆኑት የግል ሚዲያዎች አንዱ የሆነው የኢቢኤስ (EBS TV) መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አማን ፍስሃጽዮን ባደረባቸው ሕመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው የካቲት 4 ቀን 2018 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።
የኢቢኤስ ቴሌቪዥን ማኔጅመንት ባወጣው መደበኛ መግለጫ፣ የአቶ አማንን ሕልፈት በከፍተኛ ሐዘን አረጋግጧል። ተቋሙ በመግለጫው ላይ “ለኢትዮጵያ ሚዲያ ዕድገትና ለጣቢያችን ኢቢኤስ ስኬት የማይተካ ሚና የተጫወቱት፣ የታላቅ ራዕይ ባለቤት የሆኑት ብርቱ ሰው ዛሬ እንደ ቤተሰብም እንደ ጣቢያ ብናጣም፣ የአቶ አማን ፍስሃጽዮን ራዕይ ይቀጥላል” ሲል ገልጿል።
አቶ አማን ፍስሃጽዮን በኢትዮጵያ የሚዲያ ኢንዱስትሪ ውስጥ ዘመናዊና አዝናኝ የሆኑ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን በማስተዋወቅ ረገድ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ናቸው።
በተለይም እ.ኤ.አ. በ2008 በዩናይትድ ስቴትስ ሲልቨር ስፕሪንግ ሜሪላንድ ውስጥ የኢቢኤስ ቴሌቪዥንን በመመሥረት፣ በውጭ የሚኖረውን ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊ ከአገሩ ባህልና ዜና ጋር ለማገናኘት ትልቅ ድልድይ ሆነዋል።
ጣቢያው ወደ ኢትዮጵያ በስፋት በመግባት በርካታ ወጣት የሚዲያ ባለሙያዎችን፣ አቅራቢዎችንና የኪነ-ጥበብ ሰዎችን ወደ አደባባይ አውጥቷል። በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የይዘት አቀራረብ ላይ የከፍተኛ ጥራት (High Definition – HD) ስርጭትንና ዘመናዊ የቶክ ሾው ስልቶችን በማስተዋወቅ ረገድ አሻራቸው የጎላ ነው።
አቶ አማን “ለኢትዮጵያ የሚዲያ ነፃነትና ዕድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረከቱ፣ በሥራቸው ደግሞ ለብዙዎች አርአያና አበረታች የነበሩ ሰው ናቸው” በሚል በሥራ ባልደረቦቻቸውና በአድናቂዎቻቸው ዘንድ ሲገለጹ ቆይተዋል።
