በኢፌዴሪ የገቢዎች ሚኒስቴር በመካከለኛ እና ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ዘንድ እየታየ የመጣውን የዜሮ፣ የኪሳራ እና የክሬዲት ሪፖርት አቅራቢዎች ቁጥር መጨመር ለመግታት የሚያስችል አዲስ ስልታዊ እቅድ እየተዘጋጀ መሆኑ ታወቀ።
ካፒታል ጋዜጣ ባገኘው መረጃ መሰረት፣ “የግብር ተገዢነት ማሻሻያ እቅድ” የተሰኘው ይህ ሰነድ፤ የግብር ክፍያ አፈጻጸም መቀነስን ለመታደግ እና የግብር ስወራ ስጋቶችን በዘላቂነት ለመፍታት ታስቦ የተዘጋጀ ነው።
ይህ አዲስ መዋቅራዊ እቅድ በዋናነት የግብር ፋይሊንግ እና የክፍያ ተገዢነትን በጥብቅ መከታተልን፣ የተጨማሪ እሴት ታክስ ተመላሽ ቁጥጥርን ማጠናከርን፣ በከፍተኛ እና በመካከለኛ ግብር ከፋዮች ላይ ያተኮረ የንግድ ስጋት ትንተና ማካሄድ እና ግዴታቸውን በማይወጡ ግብር ከፋዮች ላይ የሚወሰዱ አስተዳደራዊ እርምጃዎችን ማካተትን ትኩረት አድርጓል።
የዝግጅት ሂደቱ ኤ.ኤ.አ እስከ ሰኔ 2026 መጨረሻ ድረስ ተጠናቆ እንዲፀድቅ የሚቀርብ ሲሆን፣ እቅዱ ከጸደቀ በኋላም እስከ ታህሳስ 2026 መጨረሻ ድረስ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲሆን መመሪያዎች እና የአሰራር ትዕዛዞች ለሚመለከታቸው የስራ ክፍሎች እንደሚተላለፉ ካፒታል ለመረዳት ችሏል።
ይህንን የቁጥጥር እቅድ ውጤታማ ለማድረግ ሚኒስቴሩ ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር ነባሩን የሲግታስ ሶፍትዌር የሚተካ አዲስ የቴክኖሎጂ ስርዓት በመገንባት ላይ እንደሚገኝ ታዉቋል።
ይህ ስርዓት የኤሌክትሮኒክ ደረሰኝ አጠቃቀምን በማስፋፋት የግብር ከፋዮችን ትክክለኛ ገቢ በቅርበት ለመከታተል ያስችላል ተብሏል።
መንግስት ይህንን እርምጃ ለመውሰድ የተገደደው በሀገራዊ የመካከለኛ ዘመን የገቢ ስትራቴጂ የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት እና የታክስ ስርዓቱን ፍትሃዊነት ለማረጋገጥ መሆኑ ተገለፀ ሲሆን በተለይም ትርፍ እያገኙ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች ኪሳራ ወይም ዜሮ ገቢ ሪፖርት የሚያደርጉ ተቋማትን ተጠያቂ ለማድረግ አዲሱ እቅድ ትልቅ ድርሻ ይኖረዋል ተብሎ ይጠበቃል።
