ጉግል በመጪው የአውሮፓውያን ዓመት በሰው ሠራሽ አስተውሎት (ኤአይ) የሚሠራ ‘ ዐይን ላይ የሚደረግ ኮምፒውተር’ የተባለ ስማርት መነጽር ለገበያ እንደሚያቀርብ አስታወቀ።
ከዚህ ቀደም ስማርት መነጽር ለማቅረብ ያደረገው ጥረት ባይሳካም በቅርቡ እንደ አዲስ መነጽሩን የሚያስተዋውቅ ይሆናል።
ጉግል በአውሮፓውያኑ 2013 መነጽሩን ሲያስተዋውቅ የወደፊቱ ቴክኖሎጂ ማሳያ ተደርጎ ተወስዶ ነበር። መነጽሩ ከዐይን በላይ ጎልቶ የሚታይ ስክሪን የተገጠመለትም ነበር። መነጽሩ በ2015 (እ.ኤ.አ) ከገበያ ውጪ ቢደረግም አሁን ግን በድጋሚ ለማቅረብ ጉግል ወስኗል።
ሜታ ባለፈው ዓመት የካቲት ላይ ስማርት መነጽር ያስተዋወቀ ሲሆን፤ ሁለት ሚሊዮን ሰዎች ገዝተውታል።
የጉግል ስማርት መነጽር ከሌሎች የጉግል ምርቶች ጋር የተሳሰሩ ናቸው። መነጽሩን የሚያደርጉ ሰዎች እንደ ጄምኒ ያሉ የጉግል መተግበሪያዎችን መጠቀም ይችላሉ። ጄምኒ በጽሑፍና በድምጽ ለጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥ የጉግል ቻትቦት ነው።
ጉግል ለገበያ ከሚያቀርባቸው መነጽሮች አንደኛው ስክሪን የሌለው ሲሆን፤ ሌላኛው ደግሞ በመነጽሩ ሌንስ ላይ ስክሪን የተገጠመለት ነው።
የቴክኖሎጂ ተንታኝ ፓውሎ ፔስካቶሬ፤ “ጉግል ከቀደመው ስህተት መማር አለበት። ከዚህ ቀደም መነጽሩን ያስተዋወቀው መውጣት ከነበረበት ጊዜ ቀድሞ ነው” ብለዋል።
ጄምኒ ቻትቦት ስኬታማ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ የጉግል ስማርት መነጽር ውጤታማ ሊሆን እንደሚችልም ተናግረዋል ሲል ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
