ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በ3.6 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የገዛትን አዲስ ዘመናዊ አውሮፕላን በዛሬው ዕለት በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተረክቧል፡፡
አውሮፕላኗ 14 ሰው የመያዝ አቅም ያላት ሲሆን የተደራጀ የአውሮፕላን ማረፊያ በሌለባቸው ገጠራማ አከባቢዎች በቀላሉ ማረፍ እንደምትችልም ፤ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ እህት ኩባንያ የሆነው ትራንስ ኔሽንስ ኤር ዌይስ ሥራ አስኪያጅ አቶ አሚር አብዱልወሃብ ለኢቢሲ ዶትስትሪም ተናግረዋል፡፡
“ሴስና ካራቫን ኤክስ” የሚል ስያሜ ያላት አዲሷ አውሮፕላን ሚድሮክ በማዕድን እና በእርሻ ዘርፍ የሚሰራቸው ሥራዎችን ለማሳለጥ ተጨማሪ አቅም እንደምትፈጥርም ጠቁመዋል፡፡
በተጨማሪም አውሮፕላኗ በኮንትራት ለጎብኚዎች እና ለአገልግሎት ፈላጊዎች የቻርተር አገልግሎት እንደምትስጥም አመላክተዋል፡፡
አውሮፕላኗ በአሜሪካው የአውሮፕላን አምራች ድርጅት ቴክስትሮን አቪዬሽን (Textron Aviation) ኩባንያ መሰራቷንም አመላክተዋል፡፡
