ሩስያ እና ሰሜን ኮሪያ ተፈጥሯዊ ድንበራቸው በሆነው የቱመን ወንዝ ላይ ሁለቱን ሀገራት የሚያገናኛቸውን የመጀመሪያውን የድልድይ መንገድ መገንባት ጀምረዋል።
የመንገድ ፕሮጀክቱ እየተጠናከረ የመጣው የሁለቱ ሀገራት አጋርነት መገለጫ ምልክት ነው ብለዋል ሀገራቱ።
የሩስያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሚኻይል ሚሹስቲን ፕሮጀክቱን ይፋ ባደረጉበት ወቅት እንዳሉት፥ መንገዱ የትራንስፖርት ወጪን ከመቀነስ በተጨማሪ በሁለቱ ሀገራት መካከል ንግድ እና ቱሪዝምን ያሳልጣል።
“ይህ በእርግጥም የሩስያ-ኮሪያ የሁለትዮሽ ግንኙነትን ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር ፕሮጀክት ነው”
ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሰሜን ኮሪያ ህዝባዊ ጠቅላይ ጉባኤ ሊቀመንበር ፓክ ታኤሶንግ ጋር በነበራቸው የቪዲዮ ውይይት።
ከምህንድስና ልህቀትነቱ ባሻገር ፋይዳው የጎላ ነው፤ በወዳጅነት ላይ የተመሰረተ መልካም ጉርብትናችንን ለማጠናከር እና ቀጣናዊ ትብብርን ለማጎልበት ያለንን የጋራ መሻት ያንጸባርቃል ብለዋል።
በቱመን ወንዝ ላይ ግንባታው ከተጀመረው የድልድይ መንገድ በተጨማሪ እየዛገ ያለ የሶቪዬት ዘመን የባቡር ሐዲድ ድልድይ ይገኛል።
አዲሱ የድልድይ መንገድ ከአንድ ዓመት ተኩል በኋላ ሲጠናቀቅ ደግሞ በሁለቱ ሀገራት መካከል ባነሰ የትራንስፖርት ወጪ የበለጠ የገቢ ወጪ ምርት ልውውጥ እንዲሁም የተሻለ የቱሪስት ፍሰት እንዲኖር ያስችላል ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር ሚኻይል ሚሹስቲን።
