የሱዳን ጦር ሠራዊት (SAF) ካርቱም ከተማ የሚገኘውን ቤተመንግሥት በመቆጣጠር በሁለት ዓመቱ የርስ በርስ ጦርነት ወሳኝ የተባለውን ድል መቀዳጀቱ ተነገረ ። የሱዳን መንግሥታዊ ቴሌቪዥን ጦሩ ቤተመንግሥቱን ያስለቀቀው ከፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ (RSF) መሆኑን ዛሬ ማለዳ ዘግቧል ። ፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ቤተመንግሥቱን ጨምሮ የሱዳን በርካታ ሰፈሮችን ለበርካታ ጊዜያት ተቆጣጥሮ ነበር ።
በሁለቱ የሱዳን ኃይላት መካከል ጦርነቱ ከዛሬ ሁለት ዓመት ግድም ማለትም (ሚያዝያ 7 ቀን፣ 2015 ዓ.ም) ከተቀሰቀሰ በኋላ ቤተመንግሥቱ ወዲያውኑ በፈጥኖ ደራሹ ኃይል ቁጥጥር ወድቆ ነበር ። ይህ ድል ለሱዳን ጦር ሠራዊት ታላቅ እመርታ እንደሆነ ቢገለጥም፤ ፈጥኖ ደራሹ ኃይሉ የካርቱም ደቡባዊ ክፍልን እና በዋና ከተማዪቱና ተጎራባቿ ኦምዱርማን ከተማ መካከል ያሉ ቦታዎችን አሁንም እንደተቆጣጠረ መሆኑ ተዘግቧል ።
ሁለት ዓመት በተጠጋው የሱዳን የርስ በርስ ጦርነት ከ28,000 በላይ ሰዎች መገደላቸውን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዘግቧል ። ከሦስት ሚሊዮን በላይ ሰዎች ተፈናቅለዋል ። ጦርነቱ በፈጠረው ረሐብ የተነሳ አንዳንድ ቤተሰቦች በሕይወት ለመቆየት ሣር እየበሉ መሆናቸውን የፈረንሣይ ዜና አገልግሎት (AFP) ዘግቧል ።
