በመቐለ ከተማ በሚገኙ 15 ነዳጅ ማደያዎች በቂ የነዳጅ አቅርቦት በማስገባት አገልግሎት እየተሰጠ የነበረ ሲሆን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ወደ ትግራይ ይገባ ነበረ ነዳጅ መቆራረጡን ተከትሎ በተፈጠረ የአቅርቦት ችግር ህገወጥ የነዳጅ ግብይትና ምርትን የመደበቅ ተግባራት መበራከታቸውን የመቐለ ከተማ ምክትል ከንቲባ የሆኑ አቶ ኤልያስ ካህሳይ ገልፀዋል።
ምክትል ከንቲባው ይህን ተከትሎ በመቐለ ከተማ አራት ክፍለ ከተሞች በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ 17 ሺ ሊትር በህገወጥ መንገድ የተከማቸ ነዳጅ በቁጥጥር ስር መዋሉን አስታውቀዋል።
ከዚህ ባሻገር የመሰረታዊ ሸቀጦች የዋጋ ንረት በከተማይቱ ስለመኖሩም በቅኝት ማረጋገጣቸው የገለፁት አቶ ኤልያስ ያልተገባ ትርፍን ለማግኘነት የሚሹ ነጋዴዎች የአቅርቦት እጥረት በሌለበት ሁኔታ በምግብ ዘይትና በሌሎች መሰረታዊ ሸቀጦች የተጋነነ የዋጋ ጭማሪ መኖሩንና ይህንን አድርገው በተገኙ ነጋዴዎች ላይም የንግድ ተቋም እስከማሸግ የሚደርስ እርምጃ መወሰድ መጀመሩን መናገራቸዉን ብስራት ሬዲዮ ሰምቷል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ በተመሳሳይ ሰው ሰራሽ የዋጋ ንረትና ምርትን በመደበቅ ስራ ተሰማርተው የተገኙ የአይደር፣ ዓዲ ሓቂ፣ ቀዳማይ ወያነና በኩሓ ክፍለ ከተማ በንግድ ስራ የተሰማሩ ስድስት ግለሰቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸው የገለፁት ምክትል ከንቲባው ምርትን በመደበቅ የዋጋ ንረት እንዲፈጠር እያደረጉ ያሉትን ተከታትሎ በህግ ተጠያቂ ለማድረግ ድንገተኛ ፍተሻዎቹ ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።
