ዩናይትድ ስቴትስ እና ኢራን በሰላም ድርድሩ ማዕቀፎች ላይ መስማማታቸውን እና የመጀመርያ ደረጃ ስምምነቱን በ24 ሰዓታት ውስጥ እንደሚፈራረሙ ፓኪስታን አስታወቀች።
የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሻህባዝ ሻሪፍ ቅዳሜ ዕለት እንዳሉት ከሆነ ከሦስት ወር በላይ የዘለቀውን ጦርነት ለማስቆም የሚያስችለው የመጀመሪያ ደረጃ የሰላም ስምምነት በሚቀጥሉት 24 ሰዓት ውስጥ ይፈረማል።
የአደራዳሪዋ ፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሻሪፍ የፊርማ ስነ ስርዓቱ በኤሌክትሮኒክስ እንደሚሆን እና በሚቀጥለው ሳምንት የሁለቱ አገራት ባለሥልጣናት ዝርዝር ጉዳዮች ላይ ውይይት እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።
አሜሪካ እና ኢራን አርብ ዕለት ለስምምነት መቃረባቸውን የተናገሩ ሲሆን የዩኤስ ባለሥልጣናት ሁለቱም በጽሑፍ ደረጃ መግባባታቸውን እና ዋሺንግተን የመጀመርያ ደረጃ ስምምነቱን በሚቀጥሉት ቀናት እንደምትፈርም ተናግረው ነበር።
ሻሪፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ “ከምን ጊዜውም በበለጠ ወደ ሰላም ስምምነት ተቃርበናል። በሚቀጥሉት 24 ሰዓታት ውስጥ የቀሩ ነገሮችን እናጠናቅቃለን፤ ፓኪስታን ከዚያ ቀጥሎ ወዲያውኑ በኤሌክትሮኒክስ እንዲፈረም ታደርጋለች፤ በሚቀጥለው ሳምንትን በቴክኒክ ደረጃ ውይይቱ ይቀጥላል” ሲሉ ጽፈዋል።
“ይህ ታሪካዊ የሰላም ስምምነት ዘላቂ ለሆነ ሰላም መሠረት እንደሚጥል እንተማመናለን።”
የኢራን ጦርነት የተቀሰቀሰው የካቲት 21 2018 ዓ.ም. እስራኤል እና ኢራን በጥምረት ቴህራን ላይ ድብደባ ከፈጸሙ በኋላ ነው።
በምላሹም ኢራን በባሕረ ሰላጤው በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮች ላይ ድብደባ ፈጽማለች። የሄዝቦላህ ታጣቂዎችም አጋርነታቸውን ለማሳየት ወደ ኢራን ሮኬቶችን አስወንጭፈዋል።
