ለሁለት ዓመታት በዘለቀውና በመቶ ሺዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች ህልፈት ምክንያት በነበረው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በጦር ወንጀልና በሰብአዊነት ላይ ለተፈጸሙ ወንጀሎች ተጠያቂ ናቸው በተባሉ 12 የኢትዮጵያና የኤርትራ የሲቪል እና ወታደራዊ ከፍተኛ ባለስልጣናት ላይ ክስ ተመሰረተ።
ክሱን በጀርመን የፌዴራል ፍርድ ቤት የመሰረቱት ከጦርነቱ በህይወት የተረፉ ስምንት ሰዎች ናቸው።
የሁለቱ ሃገራት የሲቪልና ወታደራዊ ባለስልጣናት ላይ ክሱ የቀረበባቸው በሁለት ዓመታቱ የጦርነት ጊዜ በትግራይ ክልል ለተፈጸመው ግፍና ወደ ክልሉ የሰብአዊ ርዳታ እንዳይገባ በማገዳቸው ነው ተብሏል።
ይህንኑ ተከትሎ ከጦርነቱ በህይወት የተረፉ ናቸው የተባሉ ስምንቱ ሰዎች “በግጭቱ ወቅት 12 የኢትዮጵያና የኤርትራ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናትና የጦር መኮንኖች የጦር ወንጀል እና በሰብአዊነት ላይ ወንጀል መፈጸማቸውን በመግለጽ፣ ለጀርመን ፌደራል አቃቤ ህግ ከባድ የወንጀል ክስ አቅርበዋል” ሲል ሌጋል አክሽን ወርልድ ዋይድ የተባለ ለትርፍ ያልተቋቋመ ግብረ ሰናይ ድርጅት ዛሬ አስታውቋል።
ክሱ የተመሰረተባቸውን ባለስልጣናት ማንነት በተመለከተ ግን መቀመጫውን ስዊስ ያደረገው ድርጅቱ ለጊዜው ይፋ አላደረገም። በክሱ ውስጥ የሁለቱ ሃገራት መሪዎች ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድና ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ይካተቱ አይካተቱ ድርጅቱ ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ አልሰጠበትም።
ክሱ ጀርመን ውስጥ መከፈቱ የዓለማቀፉን የወንጀል ህግ መሰረት አድርጎ ነው ያለው ዘገባው፤ ወንጀለኞች ጥፋቱን የትም ይፈጽሙ የት ሂደቱ ለፍርድ እንዲቀርቡ ያስችላል ብሏል።
የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ከአዲስ አበባና አስመራ ምላሽ ለማግኘት ያደረገው ጥረት አለመሳካቱንም በዘገባው አመልክቷል።
