በቅርስነት የሚመዘገቡ አዳዲስ ቅርሶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመሩ መምጣታቸውን የኢትዮጵያ ቅርስ ባለሥልጣን አስታውቋል፡፡
በባለሥልጣኑ የቅርስ ምዝገባ ጥናት ደረጃ ምደባ እና ቁጥጥር መሪ ሥራ አስፈጻሚ አበራ አንችሎ፤ ቅርሶችን የሚዳሰሱ፣ የማይዳሰሱ፣ ቋሚ እና ተንቀሳቃሽ የሚለውን በመለየት በቅርስነት ለማስመዝገብ በ10 ዓመት የልማት ዕቅድ እና በ5 የእስትራቴጂክ ዕቅድ ውስጥ አካቶ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
መሪ ሥራ አስፈፃሚው አክለውም ከማይዳሰሱ ቅርሶች መካከል በአፋር እና ሶማሌ ክልል ያልተጻፈ የዳኝነት ሥርዓት የተመዘገበ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ የመልካ ቁንጥሬ ባልጩት፣ በሀረር የሸዋል ኢድ በዓል በቅርቡ በቅርስነት መመዝገባቸውን እንዲሁም የወላይታ ብሄረሰብ የዘመን መለወጫን ጨምሮ ሌሎችን ለማስመዝገብ በሂደት ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
የቅርስ ምዝገባ ሂደቱ በሁለት ዓመት አንድ ጊዜ ሲሆን፤ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም /ዩኔስኮ/ እየተገመገመ የሚወሰን መሆኑን አስረድተዋል።
እንደ ሀገር ሁሉም ማህበረሰብ በቅርሶች አያያዝ እና አጠባበቅ ላይ ያለው ግንዛቤ እኩል አለመሆኑ፣ በማወቅም ባለማወቅም ቅርሶች ለሕገ ወጥ ዝውውር ተጋላጭ መሆናቸው እንዲሁም ብዙ ቅርሶች ሙሉ በሙሉ ተመዝግበው አለማጠናቀቃቸው በዘርፉ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮች መሆናቸውንም አቶ አበራ ጠቁመዋል።
