አቃቤ ሕግ በተከሳሾች ላይ ባቀረበው የፎረንሲክና ቴክኒካዊ ማስረጃዎች ላይ የቀረበውን የሰነድ አስተያየት መነሻ በማድረግ፣ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ ፀረ-ሽብር ችሎት ለጥር 28 ቀን 2018 ዓ.ም ቀጠሮ መሰጠቱን የተከሳሾች ጠበቃ ሰለሞን ገዛኸኝ አስታወቁ።
የዮሐንስ ቧያሌው፣ የክርስቲያን ታደለ እና የአማረ መለስን የችሎት ውሎ በተመለከተ ጠበቃቸው እንደገለጹት፤ በዋለው ችሎት አቃቤ ሕግ ካቀረባቸው የፎረንሲክ ማስረጃዎች ጋር በተያያዘ የተከሳሾች የሰነድ አስተያየት የቀረበ ሲሆን፣ ችሎቱም በዚህ ላይ የአቃቤ ሕግን ምላሽ ለመጠባበቅ ቀጠሮ ሰጥቷል።
ያለመከሰስ መብት ክርክር በችሎቱ ላይ በተከሳሾች በኩል “ያለመከሰስ መብታችን ስለመነሳቱ የቀረበ ማስረጃ የለም” የሚል ጠንካራ መከራከሪያ መቅረቡን ጠበቃው አስረድተዋል። ዮሐንስ ቧያሌው የአማራ ክልል ምክር ቤትና የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባል መሆናቸውን የጠቀሱት ጠበቃው፤ ከሁለቱም ምክር ቤቶች መብታቸው መነሳቱን የሚያረጋግጥ ቃለ-ጉባኤ እንዲቀርብ መጠየቃቸውን ገልጸዋል።
በተመሳሳይ ክርስቲያን ታደለ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል በመሆናቸው፣ መብታቸው የተነሳበት መንገድ ሕጋዊ አካሄዱን የተከተለ ባለመሆኑ የምክር ቤቱ ቃለ-ጉባኤ እንዲመጣ እንዲሁም የዶ/ር ካሳ ተሻገርን ጨምሮ ሌሎች ተዛማጅ የጽሑፍ ክርክሮች ለችሎቱ መቅረባቸው ታውቋል።
የጤና ሁኔታና የሕክምና ትዕዛዝ በተመለከተ ደግሞ ተከሳሾች ካቀረቧቸው የሕክምና አቤቱታዎች መካከል፣ ዮሐንስ ቧያሌው በግል ሆስፒታል የመታከም መብታቸው እንዲከበር በጠየቁት መሠረት፤ ፍርድ ቤቱ በዳኑ ሆስፒታል ሄደው እንዲታከሙ ትዕዛዝ ሰጥቷል።
በሌላ በኩል ተከሳሽ አማረ መለስ “በአዕምሮ ሕመም ምክንያት ችሎቱን መከታተል የማይችሉ በመሆናቸው ሕክምና እንዲያገኙ” የቀረበውን አቤቱታ ተከትሎ፤ ማረሚያ ቤቱ ሕክምና እየሰጠ መሆኑን ገልጿል። ፍርድ ቤቱም ማረሚያ ቤቱ የታካሚውን የሕክምና ውጤት ለችሎቱ እንዲያሳውቅ ትዕዛዝ በማስተላለፍ አጠናቅቋል።
በዛሬው የችሎት ውሎ ከሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች አያያዝ ጋር የተያያዘ አዲስ አቤቱታ እንዳልቀረበ ጠበቃ ሰለሞን ገዛኸኝ አረጋግጠዋል።
ለአዲስ ማለዳ
