በኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ኢትዮ ቴሌኮምና ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፣ ልዩ ልዩ የገጠርና የጠረፍ አካባቢዎችን የቴሌኮሙዩኒኬሽንና የፖስታ አገልግሎት ተጠቃሚ ለሚያደርገው የሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ፈንድ (Universal Access Fund)፣ ከሚያገኙት ያልተጣራ ዓመታዊ ገቢያቸው ላይ 1.5 በመቶ እንደሚከፍሉ የኢትዮጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን አስታወቀ፡፡
የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬከተር አቶ ሚሊዮን ኃይለ ሚካኤል እንደገለጹት ይህንን ተፈጻሚ ለማድረግ በኢትዮጵያ የኮሙዩኒኬሽን አዋጅ ቁጥር 1148/2011 መሠረት፣ የሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ፈንድ የገቢ መጠን ምንጭና ስለሚተዳደርበት ሁኔታ መወሰን የሚያስችል ደንብ በቅርቡ ፀድቋል፡፡ አንዱ የፈንዱ ምንጭ የቴሌኮም አገልግሎት ከሚሰጡ ኩባንያዎች ያልተጣራ ዓመታዊ ገቢ ላይ የሚሰበሰብ 1.5 በመቶ ዓመታዊ መዋጮ መሆኑን ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ኢትዮ ቴሌኮምና ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ተመሳሳይ ክፍያ እንደሚፈጽሙ ጠቁመዋል።
ኩባንያዎቹ ዓመታዊ በጀታቸውን በዘጉ በአጭር ጊዜ ውስጥ መዋጮውን ገቢ ማድረግ እንዳለባቸውና በአግባቡ በማይከፍሉት ላይ ግን ቅጣቶች እንደሚወሰዱ ገልጸው ለአንድ ወር ክፍያውን ያዘገየ ኩባንያ ዓመታዊ 1.5 በመቶ ወጪው እንደተጠበቀ ሆኖ የዚህን ክፍያ ሁለት በመቶ ጭማሪ እንዲከፍል እንደሚደረግ፣ ይህም ለተከታታይአምስት ወራት ካልተከፈለ ጭማሪው በአምስት በመቶ እየጨመረ እንደሚሄድ አስታውቀዋል። ክፍያው ሳይፈጸም ስድስት ወራት የሚሞላ ከሆነ ግን የኩባንያው ፈቃድ እንደሚሰረዝ ተናግረዋል።
