በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዋና ከተማ ኪንሻሳ የጣለው ከባድ ዝናብ ከፍተኛ የሆነ የጎርፍ አደጋ በመከሰቱ 30 ሰዎች ህይወታቸውን ያጡ ሲሆን ቤቶችና መንገዶች ወድመዋል። የክልሉ ጤና ሚኒስትር ፓትሪየን ጎንጎ የሟቾችን ቁጥር የተገለፀው ጊዜያዊ መሆኑን አፅንዖት በመስጠት ሊጨምር እንደሚችል አስጠንቅቀዋል። አስብዛኛው የሞት አደጋ ያጋጠመው በግንብ መደርመም ነው ሲሉም አክለዋል።
ወደ 17 ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች የሚኖሩባትን ከተማ አቋርጦ የሚሄደው የንድጂሊ ወንዝ አርብ ምሽት ግስቡን በማፈራረስ ዋናውን ብሄራዊ መንገድ አጥለቅልቋል። አሽከርካሪዎች ለሰዓታት ታግተው የቆዩ ሲሆን አንዳንዶቹ ሌሊቱን ሙሉ በመኪናቸው ውስጥ አሳልፈዋል። የኪንሻሳ ነዋሪ የሆነችው ፓትሪሺያ ሚኮንጋ ለሮይተርስ የዜና ወኪል እንደተናገረችው “ትላንትና ምሽት ጓደኛዬን ለመቀበል ከአየር መንገዱ ወደ ቤት ስንመለስ መኪናው ውስጥ አደርን ምክንያቱም ምንም አይነት የመኪና ማቆሚያ ቦታ ስላልነበረ ነው” ስትል ተናግራለች።
በርካታ ሰፈሮች የኤሌክትሪክ ኃይል በመቋረጡ በጨለማ ውስጥ ለማሳለፍ ተገደዋል። ሌሎች ደግሞ በውሃ እጥረት እየተቸገሩ ይገኛል። የኪንሻሳ ገዥ ዳንኤል ቡምባ ሉባኪ የውሃ መሠረተ ልማት ተጎድቷል ነገር ግን አቅርቦቱ በቀናት ውስጥ እንደሚመለስ ለነዋሪዎች አረጋግጠዋል። በመንግስት ቴሌቪዥን ላይ በሰጡት መግለጫ ለሞቱት ሰዎች ህገ-ወጥ ቤቶችን ተጠያቂ ያደረጉ ሲሆን ባልታቀደ ሰፈራ የሚኖሩ ሰዎች ከመኖሪያ ስፍራቸው ሊፈናቀሉ እንደሚችሉ አስጠንቅቀዋል።
