በ2017 በጀት ባለፉት ስምንት ወራት 22 ነጥብ 5 ቶን ወርቅ ለውጪ ገበያ ማቅረቡን የማዕድን ሚኒስቴር አስታወቀ። የኢንዲስትሪና ማዕድን ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የማዕድን ሚኒስቴርን የስምንት ወር የዕቅድ አፈጻጸም ገምግሟል።
የማዕድን ሚኒስትር ኢንጅነር ሀብታሙ ተገኘ፤ ባለፉት ስምንት ወራት 22 ነጥብ 5 ቶን ወርቅ ለውጪ ገበያ መቅረቡን ለኢንዲስትሪና ማዕድን ጉዳዮች ቋሚ ኮሜቴ ባቀረቡት ሪፖርተር ገልጸዋል። በስምንት ወራት ውስጥ ስድስት ቶን ወርቅ ለውጪ ገበያ ለማቅረብ ታቅዶ እንደነበር ጠቅሰው፤ 22 ነጥብ 5 ቶን ወርቅ ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል።
ለውጪ ገበያ እየቀረበ ያለው የወርቅ ምርት አሁን ባለበት ሁኔታ ከቀጠለ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ 33 ቶን ወርቅ ይደርሳል ያሉት ሚኒስትሩ፤ ይህም ኢትዮጵያን ከፍተኛ ወርቅ ለውጪ ከሚያቀርቡ የአፍሪካ ሀገራት ተርታ የሚያሰልፍ ነው ብለዋል።
የወርቅ ምርት በኩባንያዎችና በባህላዊ መንገድ እየተመረተ መሆኑን የገለፁት ሚኒስትሩ፤ ከተመረተው ወርቅ 95 በመቶ የሚሆነው በባህላዊ መንገድ የተመረተ መሆኑን ገልጸዋል።
ባለፋት ስምንት ወራት ከማዕድን ዘርፍ ወጪ ንግድ ከተገኘው አንድ ነጥብ 88 ቢሊዮን ዶላር ትልቁን ድርሻ ይይዛል ተብሏል።
