ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ አገልግሎት በጀመረ በአራት ዓመታት ውስጥ፣ በሀገሪቱ ዙሪያ ያሉ የ90 ቀናት ንቁ ደንበኞቹ ቁጥር 10 ሚሊዮን መድረሱን ገልጿል። ባለፉት አራት ዓመታት ተፎካካሪያችን የመንግሥት ተቋም መሆኑ ችግር ፈጥሮብናል፤ ብሏል ኩባንያው፡፡
የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዊም ቫንሄለፑት እንደተናገሩት፤ ኩባንያው በኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት መስጠት ከጀመረ አራት ዓመታትን ያስቆጠረ ሲሆን፤ በእነዚህ አራት ዓመታት ውስጥ ከ300 ቢሊየን ብር በላይ ኢንቨስት አድርጓል፡፡
የ90 ቀናት ንቁ ደንበኞች ቁጥር 10 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን፤ 7 ነጥብ 1 ሚሊዮን የሞባይል ዳታ አገልግሎት ተጠቃሚዎች መኖራቸውን ሥራ አስፈጻሚው ገልጸዋል፡፡
አሁን ላይ ኩባንያው 900 ሠራተኞች ሲኖሩት፣ ከእነዚህ ውስጥ 97 በመቶ የሚሆኑት ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን በመግለጽ፤ በተጨማሪም ከ20 ሺ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች ተዘዋዋሪ የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቁመዋል።
ሳፊሪኮም ኢትዮጵያ በየቀኑ 31 ሺ አዳዲስ የአገልግሎት ተጠቃሚ ደንበኞችን እየተቀላቀ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ካሉት ደንበኞች 75 በመቶዎቹ በቋሚነት አገልግሎቱን እየተጠቀሙ መሆኑንም ዋና ሥራ አስፈጻሚው ጨምረው ተናግረዋል፡፡
“በዚህ አራት ዓመት ውስጥ ችግር ሆኖብን የቆየው ተፎካካሪያችን በመንግሥት ባለቤትነት ያለ መሆኑ ነው” ያሉት ሥራ አስፈጻሚው፤ ሳፋሪኮም 3 ሚሊዮን ዶላር ለኢትዮ ቴሌኮም፣ ለመሠረተ ልማት ኪራይ እንደሚከፍል ጠቁመዋል፡፡ ኩባንያው የሚጠበቅበትን ግብር እስካሁኑ ሰዓት ድረስ በቴሌብር እንደሚከፍልም ነው አክለው የተናገሩት፡፡
