የቱሪዝም ዘረፉን ለማሳደግ እና ለወጣቶች የስራ እድል መፍጠር የሚችል ለማድረግ ለአስጎብኝ ድርጅቶች አስቻይ ሁኔታዎችን መፍጠር እንደሚያስፈልግ ተጠቆመ፡፡ የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት “በኢትዮጵያ ያለው የቱሪዝም አስጎብኝዎች ዘርፍ እድልና ተግዳሮቶች” ዙሪያ ከኢትዮጵያ አስጎብኝ ድርጅቶች ማህበር እና ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሂዷል። የኢትዮጵያ አስጎብኝ ድርጅቶች ማህበር ፕሬዝዳንት አንድነት ፈለቀ ከዚህ ቀደም የቱሪዝም ዘርፍ ብዙም ትኩረት ያልተሰጠው እንደነበር ጠቁመው አሁን ላይ መንግሥት ቱሪዝሙን ለማሳደግና የኢኮኖሚ አቅም እንዲኾን ከማድረግ ጀምሮ ሌሎች እየሰራቸው የሚገኙ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል ይኖርባቸውል ብለዋል። ቱሪዝሙን ለማሳደግ እና ለወጣቶች የሥራ እድል መፍጠር የሚችል ለማድረግ ለአስጎብኝ ድርጅቶች አስቻይ ሁኔታዎችን መፍጠር እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል፡፡ በዓለም ዐቀፍ ደረጃ የተከሰተው የኮሮና ቫይረስና የኑሮ ውድነት እንዲሁም በሀገር ውስጥ የተፈጠረው የሰላም መደፍረስ ቱሪዝሙን እንደጎዳው አንስተው መንግሥት ሕጋዊ የኾነውን የአስጎብኝ ድርጅት ለማበረታታት ሕገወጦችን መቆጣጠርና የሚወጡ ሕጎችን ተግባራዊ ማድረግ አለበት ሲሉም ተናግረዋል።
