በኢትዮጵያ የዕድል ሙከራ ጨዋታዎች ላይ ተሳትፎ ገቢ የሚያገኙ ሰዎች ከሚያገኙት ጠቅላላ ገቢ ላይ የሚከፍሉት የገቢ ግብር መጠን ወደ 20% (ሃያ በመቶ) ከፍ ማለቱን አዲሱ የገቢ ግብር አዋጅ ላይ ካፒታል ተመላክቷል።
ይህ ጭማሪ ቀደም ሲል በ2008 ዓ.ም. በወጣው የገቢ ግብር አዋጅ ከተደነገገው 15% የግብር ምጣኔ የጨመረ ነው።
በተሻሻለው አዋጅ መሰረት፣ በዕድል ሙከራ አሸናፊነት የተገኘው ገቢ ሲሰላ፣ ገቢውን ያገኘው ሰው ዕድሉን ለማግኘት ያወጣው ወይም የደረሰበት ማንኛውም ኪሳራ ከታክስ የሚቀነስ አይሆንም። ይህ ማለት አሸናፊዎች የሚያገኙት ጠቅላላ ገቢ ምንም አይነት ቅናሽ ሳይደረግበት ለግብር ተገዢ ይሆናል ማለት ነው።
“የዕድል ሙከራ” ተብሎ ሲገለጽ፣ የጨዋታው ውጤት በተሳታፊው ችሎታ ላይ ሳይሆን በዋነኝነት በዕድል ላይ የተመሰረተ ጨዋታን ያመለክታል። ይህ ትርጉም ሎተሪንና ቶምቦላን የመሳሰሉ የዕድል ጨዋታዎችን ያካትታል።
ይህ አዲሱ የግብር ምጣኔ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚካሄዱ የዕድል ሙከራ ጨዋታዎች ላይ ለሚሳተፉ እና ገቢ ለሚያገኙ ሁሉ ተፈጻሚ ይሆናል።
CapitalNews
