አለርት ኮምፕሬሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የህፃናት ዓይን ህክምና ማዕከል ስራ አስጀምሯል። ማዕከሉ በህፃናት ላይ የሚደርስ ዓይነ ስውርነትን በመከላከል ረገድ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው ተብሎለታል።
በማዕከሉ የምርቃት መርሃግብር ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፤ በሕፃናት ላይ የሚደርስ ዓይነ ስውርነትና የዓይን ጤና ህመም ከህፃናቱ ባለፈ ወላጅ ላይ፣ ማኅበረሰቡ እና ሀገር ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድር መሆኑን አንስተዋል።
ማዕከሉም የተሞላ የዓይን ህክምና በመስጠት የመማር፣ ማንበብ፣ መጫወት በአጠቃላይ ለህፃናቱ ከእይታ ባለፈ የወደፊት ተስፋ የሚሰጥ መሆኑን ገልፀዋል።
40 በመቶ የሚሆነው የሀገሪቱ የህዝብ ቁጥር ህፃናት መሆናቸውን ገልፀው፤ ዛሬ ላይ በህፃናት ላይ የሚሰራ ስራ ለነገ ሀገር እድገትና ብልፅግና የማይተካ ሚና ያለው መሆኑን አስታውቀዋል።
ማዕከሉም በህፃናት ላይ የሚደርስ የዓይነ ስውርነትና የዓይን ህመምን በመከላከል ረገድ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው ብለዋል።
የአለርት ኮምፕሬሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ ዶክተር ሽመልስ ገዛህኝ በበኩላቸው፤ ሆስፒታሉ የተሟላ ግብአትና ብቁ ባለሙያዋችን በመጠቀም ጥራቱን የጠበቀ የህፃናት የዓይን ህክምና በመስጠት በህፃናት ላይ የሚደርስ የዓይን ጤና እክልንና ብርሀንን በመመለስ የወደፊት ተስፋ የሚሰጥ መሆኑን ገልፀዋል።
