ላለፉት አራት ዓመታት ማዕከሉን በሀላፊነት የመሩት አቶ ያሬድ ፤« ባጋጠሙኝ አስገዳጅ ሁኔታዎች ከኦገስት 1 ቀን 2025 (ሐምሌ 25፣2017) ጀምሮ ከሃላፊነቴ እና ከድርጅቱ ለመልቀቅ መገደዴን ለማሳወቅ እወዳለሁ፡።» ሲሉ በመግለጫቸው አመልክተዋል።
ድርጅቱ አገሪቱ ውስጥ ለሚፈጽሙ የመብት ጥሰቶች፤ በተለይም በጋዜጠኞች፣ በሲቪል ማህበረሰብ አባላት እና በመብት ተሟጋቾ ላይ የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶችን በማጋለጥና መብታቸው እንዲከበር በአደባባይ በመሟገት ግንባር ቀደም ተቋም ሆኖ መቆየቱንም በመግለጫቸው ጠቅሰዋል።
ይህ እንዲቀጥል ከድርጅቱ ጠንካራ ሠራተኞችና የቦርድ አባላት ጋር በመሆን ቁልፍ ሚና ስጫወቱ መቆየታቸውንም ገልፀዋል።
ይሁን እንጅ ከአንድ አመት ወዲህ በአገር ውስጥና ከአገር ውጭ በሚገኙ ሚዲያዎች ላይ እየቀረቡ በሀገሪቱ ውስጥ ስላለው የሰብአዊ መብት ጥሰቶች በሚሰጧቸው መገልጫዎችና ማብራሪያዎች፣ እንዲሁም «በማህበረ ድህረ ገጾች ላይ ዜጎችን ስለ መብታቸው እንዲያውቁና በአገሪቱ ውስጥ ስላለው የሰብአዊ መብቶች አያያዝ በማስመልከት የማካፍላቸው ሃሳቦችና የምሰነዝራቸው የሰሉ ትችቶች በአገዛዝ ሥርአቱ ዘንድ በጥሩ ሁኔታ እየታዩ ባለመምጣታቸው የተነሳ በተለያዩ አቅጣጫዎች የተለያዩ አይነት ጫናዎችን ሳስተናግድ ቆይቻለሁ፡፡» ብለዋል።
አቶ ያሬድ አያይዘውም «የተለያዩ ዛቻዎች፣ ማስፈራሪያዎችና ትንኮሳዎችንበጸጥታ አካላት በኩል ሲፈጸሙ እንዲሁም በተንቀሳቃሽ ስልኮቼ ያልተለመዱ ጥሪዎችን ሳስተናግድ ያለውን ግልፅ ስጋትችላ በማለት በሥራዬ ላይ አተኩሬ ቆይቻለሁ፡፡» በማለት አብራርተዋል።
ሆኖም « በዚህ ሁኔታ ውስጥ በነጻነት ለመወጣትም ሆነ የተቀበልኩትን የሥራ ሃላፊነት በብቃት ለማከናወን የማልችልበት ደረጃ ላይ መድረሴን ስላረጋገጥኩ በተጓዳኝም በሥራ ጫና ብዛት ችላ ያልኳቸው የግል የጤና ጉዳዮችም ስለነበሩ እነዚህን ምክንያቶች በመጥቀስ ከወራቶች በፊት ለድርጅቱ ቦርድ የመልቀቂያ ጥያቄዬ አቅርቤ በምትኬ ሰው እንዲፈልጉ አሳውቄያለሁ፡» በማለት ገልፀዋል።
ስለሆነም ይህ መግለጫ ከወጣበት ከሀምሌ 23 ቀን 2017 ጀምሮ በማናቸውም መንገድ የሚያካፍሉት ሀሳብ የግላቸው እንጅ የድርጅቱ አለመሆኑን አቶ ያሬድ አስምረውበታል።
DW Amharic
