በአዲስ አበባ እየተገነባ የሚገኘውን አደይ አበባ ስቴዲየም ቀሪ ስራዎችን ለማጠናቀቅ 18 ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልገው ተገልጿል::አሁን የአደይ አበባ ስቴዲየም ቀሪ ስራዎችን ከሁለት አመት ባነሰ ጊዜ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው ተብሏል።
የስታዲየሙን የማጠናቀቂያ ሥራዎች ለማከናወን 18 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር መገባቱን የኢፌዴሪ ባህልና ስፖርት ሚንስቴር አስታውቋል።ግንባታውን ለማጠናቀቅ ሚንስቴር መስሪያ ቤቱ ከቻይናው ኮሙኒኬሽን ኮንስትራክሽን ድርጅት ጋር ስምምነት ተፈራርሟል።
የኢፌዴሪ ባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ የአሁኑ ስምምነት የስቴዲየሙን ምዕራፍ ሁለት ደረጃ ሁለት እና ሦስት ስራዎችን ለማጠናቀቅ የተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።ባለፉት 7 ወራት ግንባታውን ለማፋጠን ከተባበሩት አረብ ኤምሬትስ መንግስት በተገኝ የ57 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ስራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውን ያስታወሱት ሚንስትሯ ለቀሪው ስራ 18 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ውል መያዙን አሳውቀዋል።
ከኤች ኤም ኢንጂነሪግ የስቴዲየሙ ግንባታ አማካሪ መሰለ ሀይሌ (ዶ/ር) በበኩላቸው የምዕራፍ ሁለት ደረጃ ሁለት እና ሦስት ስራዎች የጣሪያ ገጠማ እና የውስጥ ስራዎችን እንደሚይዝ ተናግረዋል።የካፍ እና የፊፋን ደረጃ ባሟላ መልኩ እየተገነባ መሆኑን ያሳወቁት አማካሪው ግንባታው ከሁለት አመት ባነሰ ጊዜ እንደሚጠናቀቅም ተናግረዋል።
በተጨማሪም የስቴዲየሙ የመያዝ አቅም 60 ሺህ መሆኑ መሰለ ሀይሌ (ዶ/ር) አሳውቀዋል።የአደይ አበባ ስታዲየም ግንባታው በ2008 ዓ.ም መጀመሩ የሚታወስ ነው::
Via EBC
