በኢትዮጵያ ከታላቁ የሕዳሴ ግድብ እና ከጊቤ III ቀጥሎ 3ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው የኮይሻ የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት የመጀመሪያ ምዕራፍ የPower House የስትራክቸራል ኮንክሪት ሙሌት ሥራ በስኬት መጠናቀቁን የሲቪል መሐንዲሱ አቶ ይታገሱ አያሌው አስታውቀዋል።
ከአጠቃላይ 7.725 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የአርማታ ሙሌት ውስጥ እስካሁን ከ6.2 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ መጠናቀቁ የተገለጸ ሲሆን፣ ግንባታውን ለማፋጠን ሥራው በ2 ፈረቃ ለ24 ሰዓታት እየተከናወነ ይገኛል።
በአሁኑ ወቅት የግድቡ ቁመት 136 ሜትር የደረሰ ሲሆን፣ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ አጠቃላይ ቁመቱ 201 ሜትር እንደሚደርስና እያንዳንዳቸው 300 ሜጋ ዋት የሚያመነጩ 6 ተርባይኖች እንደሚኖሩት ተገልጿል።
ግንባታው በሚካሄድበት የስምጥ ሸለቆ አካባቢ የሚያጋጥሙ የዓለት ሁኔታዎችን ለመቋቋም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ሥራ እየተሠራ ሲሆን፣ ይህም ለሀገር ውስጥ ባለሙያዎች ከፍተኛ የቴክኖሎጂና የዕውቀት ሽግግር ፈጥሯል።
በተጨማሪም የውኃ ማስተንፈሻ በሮች ግንባታ የስትራክቸራል አርማታ ሙሌት 45 በመቶ ደርሷል። ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ የሚፈጥረው ግዙፍ ሰው ሠራሽ ሐይቅ የኃይል አቅርቦቱን ከማሳደጉ ባሻገር፣ በመንግሥት ‘ገበታ ለሀገር’ መርሐ ግብር የታገዘውን የአካባቢውን የቱሪዝም መስህብነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያነቃቃው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃን ጠቅሶ የመንግስት ሚዲያ ዘግቧል፡፡
