በአሁኑ ወቅት በምእመናን ላይ እየተከሠተ ያለውን ዘርፈ ብዙ ቀውስ ለመቀነስና ኦርቶዶክሳዊ ቤተሰብን ለማጠናከር ማኅበረ ቅዱሳን በስልታዊ ዕቅዱ በማካተት ከባለ ድርሻ አካላት የተውጣጣ ኦርቶዶክሳዊ የምክክርና የማገገሚያ ተቋማት አስፈጻሚ ኮሚቴ አዋቅሮ ቅድመ ዝግጅት እያደረገ ይገኛል ።
ይህን በጎ ዓላማ በሐሳብ ፣በሙያና በገንዘብ ለመደገፍ የሚያስችል የግንዛቤ ማስጨበጫና ማስጀመሪያ መርሐ ግብር የሚመለከታቸው የዘርፉ የሥራ ኀላፊዎች፣ በጎ አድራጊ ግለሰቦች፣ አርቲስቶችና ተፅዕኖ ፈጣሪ ሰዎች በተገኙበት በዮድ አቢሲንያ የባህል አዳራሽ ተካሄዷል፡፡
ተቋማቱን ለማቋቋም ያስፈለገበት መነሻ ምክንያት በዕለቱ እንደተገለጸው እየተከሠቱ ባሉ ተገማች ያልሆኑ ውስብስብ ችግሮች መፈጠር ምክንያት የበርካታ ወገኖች ተጋላጭነት እና ተጠቂነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል፡፡
ከአሁን በፊት በቤተ ክርስቲያን መዋቅር የሚመራና የተደራጀ መፍትሔ ሰጭ ኦርቶዶክሳዊ ተቋም አለመኖሩ ደግሞ ችግሩ እንዲባባስ አድርጎታል ፡፡
ይህን አሳሳቢ ጉዳይ በመረዳት ማኅበረ ቅዱሳን ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር በተመረጡ 11 የሀገራችን ከተሞች በአጭር ጊዜ የምክክር መስጫ ተቋማትን እና በመካከለኛ ጊዜ ዕቅድ ደግሞ 1 ከሱስ ማገገሚያ ማእከል በአዲስ አበባና በሂደትም በተመረጡት የክልል ከተሞች ለማቋቋም የጥናትና ቅድመ ዝግጅት ተግባራትን አከናውኗል፡፡
በተቋማቱ የሚሠጠው አገልግሎት በሃይማኖት ሳይገደብ መፍትሔ ለሚሹ ወገኖች ሁሉ በዘርፉ በሠለጠኑና ልምድ ባላቸው መምህራን፣ አባቶችና ባለሙያዎች በአንድ ማእከል የሚሰጥ ይሆናል፡፡
በምክክሩ አገልግሎቱ በጋብቻና ትዳር ፣በልጆች አስተዳደግ፣በጤና፣ በሥነ ተዋልዶ፣በሥነ ልቦና፣ በሥነ አእምሮ፣ በምጣኔ ሀብት፣ በሌሎች ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ጉዳዮች ትኩረት የሚደረግ ሲሆን በማገገሚያ ማእከሉ ደግሞ በከፋ ደረጃ ለሱስ ተጋላጭ የሆኑ ወጣቶች ሰብእና ግንባታ ተደርጎላቸው ዘላቂ መፍትሔ በሚያገኙበት ተግባር ላይ እንደሚሠራ በዕለቱ ተብራርቷል፡፡
የምክክር ተቋማቱን ዕውን ለማድረግ ከ12 ሚሊዮን ብር በላይ እና ለማገገሚያ ተቋሙም ከ35 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት እንደሚጠይቅ የተገለጸ ሲሆን ለዚህም በጎ አድራጊ ግለሰቦች፣ ድርጅቶችና የሚመለከታቸው ተቋማት የሙያ፣ የሐሳብ፣ የገንዘብና የዓይነት ድጋፍ በአጠቃላይ አስፈላጊውን ሁለንተናዊ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል፡፡
የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ በማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ ድጋፍ የባንክ ሒሳብ ቁጥሮች “ለምክክር አገልግሎት ተቋም” የሚል ምክንያት በመግለጽ በአሐዱ ባንክ 0025393820301
በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1000309803648
በአቢሲንያ ባንክ 37235458 መጠቀም የሚችሉ ሲሆን
ለበለጠ መረጃ በ0948506072 /በ0984181544 ይደውሉ፡፡
