በአንዳንድ አካባቢዎች በተፈጠረ የጸጥታ ችግር ምክንያት ከ7 ነጥብ 2 ሚሊየን በላይ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው አለመመለሳቸውን የትምህርት ሚኒስትሩ ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) ገለጹ፡፡
ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) እና የአማራ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት ሥራ ኃላፊዎች እና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በባሕር ዳር ከተማ የክልሉ የትምህርት ንቅናቄ መድረክ እየተካሄደ ነው።
ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር፥ በኢትዮጵያ አንዳንድ አካባቢዎች በተፈጠረ የጸጥታ ችግር ምክንያት ከ7 ነጥብ 2 ሚሊየን በላይ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዳልተመለሱ ገልጸዋል።
የአማራ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ በክልሉ በጸጥታ ችግር ምክንያት በዘንድሮው የትምህርት ዘመን 7 ሚሊየን ተማሪዎችን መዝግቦ ለማስተማር ቢታቀድም፤ የተመዘገቡት ተማሪዎች 2 ነጥብ 8 ሚሊየን ብቻ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡
ችግሩን ለመቅረፍ በትምህርት ዘመኑ በሁለት ዙር በተደረጉ ኢ-መደበኛ ምዝገባዎች የተመዘገቡት 76 ሺህ ተማሪዎች ብቻ መሆናቸውን ኤፍ ኤም ሲ ዘግቧል፡፡
