የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን ከሚያከናውናቸው የቁጥጥር ሥራዎች ውስጥ የምግብ ጥራትና ደህንነት ከመቆጣጣር አንፃር በተለይም የወተት ጥራትና ደህንነት ዙሪያ በአዳማ ከተማ ለሚዲያዎች በተሰጠ ግንዛቤ ማስጨበጫ መርኀ ግብር ላይ ወተትን በጀሪካን ማከፋፈል ትክክል ያልሆነ ተግባር መሆኑን ገልጿል።
የወተት ምርት በባህሪው ጥንቃቄ የሚፈልግ በመሆኑ በተገቢው መንገድ የቅዝቃዜውን ሰንሰለት በጠበቀ መልኩ ቀዝቃዛ ፍሪጅ የተገጠመለት ታንከርና ኮንቲነር ባለበት በጥንቃቄ መጓጓዝ እንዳለበት ተገልጿል። እንደፈለጉ ውሀ በመጨመርና እንዳይበላሽ ኬሚካል እየጨመሩ ማቆየት ለከፋ የጤና እክል እንደሚዳርግ ተነግሮ ይህን ተግባር እየፈፀሙ ያሉ አካላት ከዚህ ተግባር መቆጠብ እንዳለባቸው በአፅንኦት ተነግሯል።
በተለይም ከወተት አምራቾች ወተትን በጀሪካን እየወሰዱ እንዲሁም ከቦታ ቦታ ያለበቂ ጥንቃቄ እያንቀሳቀሱ በየቤቱ የሚያከፋፍሉ አካላት ተግባራቸው ትክክል እንዳልሆነ ሊያውቁ ይገባል ተብሏል። በተጨማሪ ባለስልጣኑ ህብረተሰቡ ጥሬ ወተትን በጥሬው ከመጠቀም ይልቅ ፓስቸራይዝ የሆኑ ምርቶችን ቢጠቀም የተሻለ እንደሆነ ጠቁሟል።
በተያያዘ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ በልዩ ትኩረት አጠቃላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የወተት አምራቾች በሙሉ የሶስትኛ ወገን የጥራት ምርመራ ሰርተፊኬትን አሟልተው ምርታቸውን ወደ ገበያ ማቅረብ እንዳለባቸው ተጠቁሟል።
የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን በአዋጅ ቁጥር 1112/2011 በተሰጠው ስልጠንና ተግባር መስረት የምግብ ጥራትና ደህንነት፣ የመድኃኒትና የህክምና መሣሪያዎች ጥራት፣ ደህንነትና ፈዋሽነትን የቁጥጥርየህክምና መሳሪያዎች ውጤታማነት የማረጋገጥ ሥራዎችን ያከናወናል፡፡
