በቱርክ መንግስት ድጋፍ ላለፉት ዘጠኝ ወራት ጥገና ሲደረግለት የነበረው በትግራይ ክልል የሚገኘው ጥንታዊው የአልነጃሺ መስጂድ እና መቃብር ቦታ እድሳት በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን የክልሉ ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ።
የክልሉ የቱሪዝም ቢሮ ምክትል ሃላፊ ሀይላይ በየነ ለአዲስ ሰታንዳርድ እንዳስታወቁት እድስታ ሲደረግላቸው የነበሩት የመስጂዱ እና መቃብሮቹ “ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ርክክብ ብቻ ነው የቀረው”።
በትግራይ ክልል በተካሄደው ጦርነት ወቅት ከፍተኛ ጉዳት አስተናግዶ የነበረው ታሪካዊው የአልነጃሺ መስጊድ እና መቃብር ቦታ በቱርክ መንግስት ተቋም በሆነው ቲካ (የቱርክ ድጋፍ ማስተባበሪያ ኤጀንሲ) ሙሉ ለሙሉ ጥገና እንደተደረገለት ተጠቁሟል።
በአፍሪካ የመጀመሪያው የሙስሊም ሰፈር ተብሎ በሚጠራው በኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ነጃሺ ከተማ የሚገኘውን የነጃሺ መቃብር እና መስጂድ ለመጀመሪያ ጊዜ እድሳት የተደረገለት በ2019 ሲሆን እድሳቱ ሳይገባደድ በክልሉ በተካሄደው ጦርነት ሳቢያ ደጋሚ ጉዳት አስተናግዶ ተጨማሪ እድሳት እንደተደረገለት ተጠቁሟል።
የክልሉ የቱሪዝም ቢሮ ምክትል ሃላፊ ሀይላይ በየነ ለአዲስ ሰታንዳርድ እንዳስታወቁት እድስታ ሲደረግላቸው የነበሩት የመስጂዱ እና መቃብሮቹ “ስትራክቸራል ክፍል ሙሉ በሙሉ አልቋል”።
“አንዳንደ የኤሌክትሪክ፣ የውሃ እና መሰል የሚሰሩ ነገሮች ነበሩ፣ እሱም አልቋል፣ ግን ቸክ መደረግ አለባቸው፣ ቸክ መደረግ ያለባቸው ነገሮች ስላሉ ነው እንጂ ሙሉ በሙሉ አልቋለ ሊባል ይችላል” ብለዋል።
“አሁን ላይ ርክክብ ብቻ ነው የሚቀረው፣ ያላለቀ ስራ የለም ማለት ይቻላል” ሲሉ ለአዲስ ስታንዳርድ የገለጹት ምክትል የቢሮ ሃላፊው “ርክክቡ ገና ቀኑ አልተቆረጠለትም፣ በልዩ በጥሩ ሁኔታ የምረቃ ስነስርአት ይካሄዳል” ሲሉ አስታውቀዋል።
እድሳት እንደተደረገለት ከተገለጹት መካከል የመቃብሩ ጉልላት፣ የመስጂዱ ሚናር፣ ለሁለገብ አገልግሎት የተገነባው የአደራሹ ግድግዳዎች እና የእንጨት ክፍሎች ይገኙበታል። በተጨማሪም በመስጂዱ እና በመቃብሮቹ አከባቢ በግዜ ብዛት እና በአየር ሁኔታ ምክንያት ብልሽት የደረሰባቸውን አከባቢዎች ለማስተካከል መቻሉም ተገልጿለ።
የቱርክ መንግስት ድጋፍ ማስተባበሪያ ኤጀንሲ (ቲካ) የአልነጃሺ መስጂድ እና መቃብር ቦታ ለትውልድ ተጠብቆ እንዲቆይ ተደርጓል ሲል ባወጣው መግለጫ አመላክቷል።
የቱሪዝም ሚኒስቴር የአልነጃሺ መስጅድ የጥገና ስራው በተጀመረበት ወቅት ባጋራው መረጃ የአልነጃሺ መስጅድ የጥገና ስራው ታሪካዊ ይዘቱን ለትውልድ ጠብቆ ማስተላለፍ በሚያስችል መልኩ የሚከናወን ይሆናል ሲል ማስታወቁን መዘገባችን ይታወሳል።
እድሳቱን በቱርክ ትብብርና ማስተባበሪያ ኤጀንሲ (ቲካ) በተቋቋመው የባለሙያዎች ቡድን ክትትል እንደሚደረግለት እና የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን እንዲሁም የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የቁጥጥር ስር እንደሚያከናውኑም በዘገባው ተጠቁሞ ነበር። አስ
