ባለስልጣኑ ባበለፀገዉ የኤሌክትሮኒክስ የግብይት ስርዓት የመንግስት ተቋማት 3መቶ 3 ቢሊየን ብር ግምታዊ ዋጋ ያላቸዉን ንብረቶች መገበያየታቸዉን አስታወቀ፡፡
ከኢትዮ ኤፍኤም ጋር ቆይታ ያደረጉት የባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ዋና ዳይሬክተር መሰረት መስቀሌ፤በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የመንግስት ተቋማት ከ3መቶ3 ቢሊዮን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸዉን ንብረቶች በኤሌክትሮኒክስ የግብይት ስርዓት ግዢ መፈጸማቸዉን ነግረዉናል፡፡
ለሙስና ከተጋለጡ አሰራሮች ውስጥ የመንግስት ግዢና ጨረታ አንዱ እንደሆነ ያነሱት ዳይሬክተሯ፤ግዢና ጨረታው ከተለመደው አሰራር ወጥቶ በኤሌክትሮኒክስ መሆኑ ከዚህ ቀደም የሚነሱ ቅሬታዎችንና ብልሹ አሰራርን ማስቀረት ተችሏል ብለዋል፡፡
ዳይሬክተሯ ስርዓቱ ምን ያህል ሙስናን እና የሃብት ብክነትን ቀርፏል የሚለዉን ለማወቅ በቀጣይ ጥናት ይደረጋል ነዉ ያሉት፡፡
የኤሌክትሮኒክስ የመንግስት ግዢ ስርዓት ተግባራዊ መሆን ከጀመረ አራት አመት መቆጠሩንም የሚያነሱት ዋና ዳይሬክተሯ፤ በዚህ ጊዜ ዉስጥ የፌደራል መስሪያ ቤቶችን እና የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎችን ጨምሮ 2መቶ35 ተቋማት በኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት ዉስጥ መካተታቸዉን አንስተዋል፡፡
ከመንግስት ተቋማት በተጨማሪም ከ24 ሺህ በላይ የንግዱ ማህበረሰብ በዚህ የግዢ ስርዓት ዉስጥ መካተታቸዉንም ነዉ የገለጹት፡፡
በዚህ ስርዓት በቀጣይ ዓመት ሁሉንም የክልል ቅርንጫፍ መስሪያ ቤቶችን ለማካተት ስራዎች እየተሰሩ እንዳሉም ወይዘሮ መሰረት ተናግረዋል፡፡
