የቻይናው ሻንሀይ ላውንች ዲዛይን አውቶሞቲቭ ኩባንያ በኢትዮጵያ ውስጥ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ የአየር ታክሲና ሰው አልባ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ ዘመናዊ ተሽከርካሪዎችን ለማምረት ፍላጎት እንዳለው አስታወቀ።
ይህንንም ፍላጎት ይፋ ያደረገው የኩባንያው ስራ አስኪያጅ ው ሻውሀን ከትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ ነው።
በውይይቱ ወቅት ሚኒስትሩ መንግስት አረንጓዴ ትራንስፖርትን ለማስፋፋት ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸው ጠንካራ የመንግስት ድጋፍ እና የታክስ ማበረታቻዎች ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎች መሆናቸውን አስረድተዋል።
የሻንሀይ ላውንች ዲዛይን አውቶሞቲቭ ስራ አስኪያጅ እንዳሉት ኩባንያቸው በኢትዮጵያ ውስጥ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በማምረት ላይ መሰማራት እንደሚፈልግ ገልጸዋል።
ኩባንያው በኤሌክትሪክ የሚሰሩ የአየር ታክሲና ሰው አልባ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ አውቶሞቢሎችን፣ አውቶብሶችንና የጭነት ተሽከርካሪዎችን እንደሚያመርትም አብራርተዋል።
