በአዲስ አበባ የሚገኘው ቬኒዙዌላ ኤምባሲ የአሜሪካ መንግሥት በቬኔዙዌላ ስደተኞች ላይ የሚፈጽመውን ማንገላታት ለማስቆም ሁሉም በሕብረት እንዲቆም ጥሪ አቅርቧል።
ይህንን ያለው አዲስ አበባ ከተማ በሚገኘው ኤምባሲው በተካሄደ ስብሰባ ላይ ነው።
“ለዚህም ሁሉም ሀገራት በስደተኞች ላይ የሚፈጸመውን ግፍ ለማስቆም በሕብረት መቆም አለባቸው” ሲሉ አምባሳደር ኤዲ ኮርዶቫ ገልጸዋል።
“ስደተኝነት ወንጀል አይደለም” ያሉት አምባሳደር ኤዲ፤ “ቬኔዙዌላ ስደተኛ ተቀባይ ሀገር ብትሆንም አሁን ግን በአሜሪካ የሚገኙ የቬኔዙዌላ ስደተኞች ላይ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እየተፈጸመ ይገኛል” ብለዋል።
“በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የቀረውን ስርዓት የአሜሪካ መንግሥት እየተገበረ ነው” ያሉም ሲሆን፤ ድርጊቱ አዲስ የፋሺዝም ስርዓት በመሆኑ ሁሉም ሊከላከለው እንደሚገባም አሳስበዋል።
የአሜሪካ መንግሥት በደቡብ አሜሪካ በምትገኘው ኤልሳልቫዶር እስረኞችን ለመውሰድ 600 ሺሕ ዶላር በወር ኪራይ ልትከፍል መስማማቷንም አምባሳደሩ አክለው ገልጸዋል።
ስደተኞችን የማጋዝ እና ሰብዓዊ መብት ጥሰት የማድረግ ነገር በቬኔዙዌላ ብቻ አይቆምም የተባለ ሲሆን፤ “በርካታ ስደተኞቿ በአሜሪካ የሚገኙባት አፍሪካ ይህንን ማውገዝ አለባት” ብለዋል።
መጠነ ሰፊ የሆነ የነዳጅ ክምችት ያላት ቬኒዙዌላ ከአሜሪካ ሰፊ የሆነ ጫና እየተደረገባት ይገኛል።
በዚህም ዶናልድ ትራምፕ ከቬንዚዌላ ላይ ነዳጅ በሚገዙ ሀገራት ላይ የ25 በመቶ ታሪፍ እንደሚጥሉ ማስታወቃቸው ይታወቃል።
