በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ፣ ከሰሞኑ ከኃላፊነታቸው በፈቃዳቸው የለቀቁትን የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ አቶ ማሞ ምህረቱ በይፋ አመሰገነ፡፡
ኤምባሲው በማህበራዊ ትስስር ገጹ ባሰፈረው መልዕክት፤ አቶ ማሞ ለሰጡት አገልግሎትና ለራዕያቸው ምስጋና አቅርቧል፡፡
“የአቶ ማሞ ድፍረት የተመላበት አመራር፣ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚና ህዝቧን ወደ ኋላ ይጎትቱ የነበሩ የማክሮ ኢኮኖሚ መዛባቶችን ለማረም ረድቷል” ብሏል፤ ኤምባሲው።
ኢትዮጵያ እሳቸው መንገድ የጠረጉለትን የኢኮኖሚ ማሻሻያ እንድትቀጥልም አሳስቧል።
ኤምባሲው አክሎም፤ “በተለይ ከባድ ተግዳሮቶች ባሉበት ሁኔታ ውስጥ ለውጥ በጭራሽ ቀላል አይደለም” ሲልም ለሪፎርሙ ዕውቅና በመስጠት የቀድሞውን የብሔራዊ ባንክ ገዢ አመስግኗል፡፡
