ይፋዊ የግብይት ማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የባንክ ፕሬዚዳንቶችና የልማት አጋሮች በተገኙበት ተካሄደ።
ወጋገን እና ገዳ ባንኮች በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ ሰነዶቻቸውን በማስመዝገብና ሌሎች መስፈርቶችን በማሟላት ግብይታቸውን በይፋ አስጀምረዋል።
የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ ግብይት መጀመሩ፥ የሪፎርም ስራዎችና የግሉ ዘርፍ ስኬት መሆኑን ተናግረዋል።
የብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምህረቱ፥ መንግስት በኢኮኖሚው ውስጥ ያጋጠሙ ችግሮችን ለመፍታት ከወሰዳቸው እርምጃዎች መካከል ጠንካራ የካፒታል ገበያ መመስረት አንዱ መሆኑን አንስተዋል።
የኢትዮጵያ የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጥላሁን ካሳሁን(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ ገበያው አስፈላጊ ዝግጅቶችና ሒደቶችን አልፎ በይፋ ግብይት መጀመሩን ገልጸዋል።
የግብይቱ መጀመር ለሀገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ ትልቅ ምዕራፍ እንደሆነም ተነግሯል።
የኢትዮጵያ የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የሰነደ ሙዓለ ነዋዮች የገበያ መድረክ ሲሆን በመንግስትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት የተቋቋመ ነው።
የገበያው ዋና ዓላማ ውጤታማ የካፒታል ማሰባሰብ ስራዎችን በማጠናከር የኢትዮጵያን ምጣኔ ሃብት እድገት ግልጽና ደህንነቱ በተጠበቀ የካፒታል ገበያ ስራዎች መደገፍ ነው።
