የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ2017 ዓ.ም በጀት ዓመት ስምንት ወራት ከ264 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር ለደንበኞች ማቅረቡን የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ ገለጹ።
717 ሺህ ደንበኞች በዲጂታል አማራጭ የብድር ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውንም አመልክተዋል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ የተቋሙን የስምንት ወራት አፈጻጸም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አቅርበዋል።
ፕሬዚዳንቱ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ባንኩ ብድርን ከማስፋፋት እና የዜጎችን የፋይናንስ ተጠቃሚነት ከማሳደግ አንፃር አዳዲስ የብድር አይነቶችን እያስተዋወቀ ይገኛል፡፡
በዚህም ባንኩ ባለፉት ስምንት ወራት ብቻ 264 ነጥብ 65 ቢሊዮን ብር ብድር ለደንበኞቹ ማቅረቡን ገልጸው ከዚህ ውስጥ 88 ነጥብ 2 በመቶው የተሰጠው ለግሉ ዘርፍ እንደሆነ አመልክተዋል።
እደ ኢዜአ ዘገባ ጠቅላላ የተሰጠ የብድር መጠን ብር 1 ነጥብ 39 ትሪሊዮን በር መድረሱንም ጠቁመዋል።
የብድር ተደራሽነትን ከማስፋት አንፃር ባንኩ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመተባበር በዲጂታል አማራጭ ብድሮችን እያቀረበ መሆኑን ነው ያስረዱት።
ፕሬዝዳንቱ በዲጂታል አማራጭ ባለፉት ስምንት ወራት አጠቃላይ ብር 3 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብድር ማቅረብ መቻሉንና በፈረንጆች እስከ ፌብሩዋሪ 28 ቀን 2025 ድረስ 717 ሺህ ደንበኞች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።
