ከ10 ዓመት በኋላ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ገቢ 25 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ መሆኑን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው ገለጹ፡፡
አቶ መስፍን ከዘመን ኢኮኖሚ ዝግጅት ክፍል ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ አየር መንገዱ እአአ በ2035 ላይ 209 ዓለም አቀፍ እና 31 የሀገር ውስጥ መዳረሻዎች፣ 271 አውሮፕላኖች የሚኖሩ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
67 ነጥበ 2 ሚሊዮን መንገደኞችንም በማጓጓዝ ከ10 ዓመት በኋላ ገቢውንም 25 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ መታቀዱን ገልጸዋል፡፡
ለዚህም አዳዲስ መዳረሻዎችን በማስፋት ትስስሩን ይበልጥ ማጠናከር እና አዳዲስ መዳረሻዎችን መክፈት የሚያስፈልግ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ለዚህም አሁን በረራ ከሚደረግባቸው አምስቱ ክፍለ አኅጉሮች ተጨማሪ አውስትራሊያንም የሚጨመር መሆኑን ጠቅሰው፤ በብዙ ሀገሮች አንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን ሁለትም ሶስትም አራትም ጊዜ በረራ ከማድረግ መታቀዱን ገልጸዋል፡፡
ያረጁትን አውሮፕላኖችን በመለወጥ አዳዲስ ዘመናዊ አውሮፕላኖች የሚመጡ መሆኑንም አንስተዋል፡፡
ጥሩ ሥነምግባር እና ተነሳሽነት ያለው ሠራተኛ መገንት መቀጠል አለበት ያሉት አቶ መስፍን፤ በየዓመቱ 300 ፓይለት ለማሰልጠን እቅድ መያዙንም አስታውቀዋል፡፡
ከአምስት ዓመት በኋላ (እአአ በ2029) ሙሉ በሙሉ ወደ አዲሱ ኤርፖርት የሚገባ መሆኑን ገልጸው፤ አዲሱ ኤርፖርት በጥራትም በስፋትም ከአፍሪካ አንደኛ በመሆን የአፍሪካን የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ከሌላው ዓለም ደረጃ ላይ እናደርሳለን ብለዋል።
ጋዜጣ_ፕላስ
